“ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አራት” በሁለት ሺህ አስራ አራቷ ኢትዮጵያ እይታ ሲገመገም፣

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ 

Meles Zenawi1 “ታላ ወንድም” በአንክሮ እየተመለከቷችሁ ነው! በሚስጥር፡ የሚንሾካሾከው ወሮበላ መንግስት በ2014ቷ ኢትዮጵያ 

በኢትዮጵያ ያለው ሚስጥር አነፍናፊው ገዥ አካል በጉአዳ ውስጥ የተደበቁ የኢትዮጵያውያንን/ትን ሚስጥሮች መርምሮ ለማውጣት በጣም ውድ የሆኑ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን በመጠቀም የስለላ ፕሮግራሞችን በመተግበር በታላቅ ፍርሀት ውስጥ ተዘፍቆ በመንፈራገጥ ላይ ይገኛል፡፡ ከፍርሀታቸው የተነሳ ህዝቡ በእነርሱ ላይ ምን ለማድረግ እንደሚችል ስጋት ውስጥ በመውደቅ እራሳቸውን በማስጨነቅ እንቅልፍ አጥተው ሲባንኑ ያድራሉ፡፡ ለመሆኑ በሚስጥር ስለኛ የሚንሾካሾኩት እነማን ናቸው? ብለው ራሣቸዉን ይጠይቃሉ:: ሰዉ ስለእነርሱ ጉዳይ ምን ሚስጥር ነው የሚያወራው? በእርግጥ ህዝቡ እነርሱ እንደሚያስቡት እና እንደሚደርጉት በሚስጥር ይዘባበትባቸዋልን? (ይህ የአደባባይ ሚስጥር ነው)፡፡ ህዝቡ በሚስጥር እየተንሾካሾከ የሙጥኝ ብለው ከያዙት የስልጣን ወንበራቸው ለማባረር ዕቅድ አለውን? ለመሆኑ ለሚስጥራዊው የሸፍጥ ስራው ተዋንያኖቹ እነማን ናቸው? የትስ ነው የሚገኙት? በኢትዮጵያ? በአውሮፓ? በአሜሪካ? ሚስጥረኞቹ የገዥው አካል ጠላቶች ተብለው የተፈረጁት ከ ጠፈር በላይ (ህዋ) ካለ ዓለም የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ይሆን?

ለገዥው አካል ዕውቀት ኃይል ነው፡፡ በፍጹም! ይልቁንስ ለእርሱ ድንቁርና ኃይል ነው፡፡ ገዥው አካል በአንድ ወይም በሌላ መልኩ ዕኩይ ምግባራትን ከመፈጸም ነጻ የሆነበትን ጊዜ ፈልጎ ማግኘት ከባድ ነገር ነው፡፡ ህዝቡን የማይደውል የስልክ ቀፎ እንዲሸከም በማድረግ ችግር በመፍጠር ላይ ይገኛል፡፡ የተንቀሳቃሽ ስልኮች እንዳይሰሩ ያደርጋል፡፡ በግል ኮምፒውተሮች ላይ ህገወጥ ምርመራ ያደርጋል፡፡ በገዥው አካል ላይ ትችት በሚያቀርቡት ድረገጾች ላይ ስለላ ያካሂዳል፡፡ ሌላስ ምን ያደርጋል? እነዚህ የዕኩይ ምግባር ባለቤቶች አዕምሯቸውን በማስጨነቅ እንቅልፍ የለሽ ሌሊቶችን የሚያሳልፉት ባለማወቅ በድንቁርና ምክንያት ብቻ አይደለም፣ ሆኖም ግን ሆን ብለው እያወቁ የሚተገብሩት እንጅ፡፡ ምን እንዳደረጉ ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ እናም ምን ያለበት እንትን አይችልም ነው እና በአሁኑ ጊዜ በእነርሱ ላይ ህዝቡ በሚስጥር ምን እንዳሰበ እና ምንስ ሊሰራ እንደሚችል ለማወቅ ይፈልጋሉ፡፡ በከንቱ ይባዝናሉ፡፡ በሌሊት ቅዠታቸው እውነት ጎራዴን ጨብጣ አፈር ድሜ ልታበላቸው ስታባርራቸው ያድራሉ፡፡ ከዚያም በላብ ተዘፍቀው ይነቃሉ፡፡ ይልቁንስ በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ያለው ደንቆሮ ወሮበላ ገዥ አካል የሌሊት ህይወት ሚስጥር ይኸ ነው ፡፡

ሚስጥራዊነት ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል የመሰረተው የጭቆና ህንጻ መገንቢያ ጡብ እና ጭቃ ነው፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ “የእነርሱ ታላቁ፣ ባለራዕይ፣ ጀግና፣ የህዳሴ ቀያሽ፣ ወዘተ መሪ“ ካረፉ ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ ጀምሮ በታላቅ የመንፈስ ጭንቀት ውስጥ ተዘፍቆ የሚገኝ ሲሆን ስለሰውየው የአሟሟት መንስኤ እስከ አሁን ድረስ አንድም ቃል በግልጽ ትንፍሽ ያሉት ነገር የለም፡፡ ይህ ሁኔታ በከፍተኛ ደረጃ በመንግስት የሚጠበቅ ሚስጥር ነው፡፡ ጫካ ከነበሩበት ጊዜ ጀምሮ አሁን መንግስትን እየመሩ እስካሉበት ጊዜ ድረስ መጥፎ የሚስጥራዊነት ባህልን እና ሙስናን (“የሚስጥረ ሙስና ባህል” በማለት እራሴ እንደምጠራው አዲስ ቃል እና ትርጉም አንባቢዎቸ እንግዳ እንደማይሆኑ አምናለሁ) ሲያራምዱ የቆዩት አስጠያፊ ባህላቸው ነው፡፡ በእርግጥ በግልጽ የሚስጥራዊነት እና ሙሰኝነት ስልቶቻቸውን ጥበብ በመጨመር አሻሽለዋቸዋል፡፡ ውሳኔዎቻቸውን በጸጥታ እና በሚስጥር ያሳልፋሉ፡፡ በአገሪቱ ላይ የሚወሰኑ ከፍተኛ እንደምታን ሊያስከትሉ የሚችሉ ውሳኔዎች የሚተላለፉት በውሱን ሚስጥር ደባቂ ምግባር የለሾች፣ ስም የለሾች እና ህሌና ቢስ የስልጣን ጥመኞች የመንግስት የቡድን አባላት (“መንግስት በመንግስት ስር የተደበቀ”) ሚስጥር አድርጎ በመያዝ ነው፡፡ የገዥው አካል ተዋንያኖች እና የእነርሱ ሎሌዎች በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ በውጭ አገር በሚገኙ የባንክ ሂሳቦቻቸው በሚስጥር አጭቀው ይገኛሉ፡፡

ግሎባል ፋይናንሻል ኢንቴግሪቲ/Global Financial Integrity የተባለው ዓለም አቀፋዊ ተቋም በቅርቡ ባወጣው ዘገባ መሰረት እ.ኤ.አ ከ2000 ጀምሮ በህገወጥ ሚስጥር የገንዘብ ዝውውር ምክንያት ኢትዮጵያ ወደ 12 ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ገንዘብ  አጥታለች፡፡ ታላላቅ የህዝብ ስራዎችን እና የፕሮጀክቶች ኮንትራቶችን የውሸት ካባ በማልበስ በድብቅ ለገዥው አካል ደጋፊዎች እና ሎሌዎች በመስጠት በሚስጥር ሙስናው ተጧጡፏል፡፡ በአገሪቱ በጣም ለም የተባለው መሬት ለሳውዲ፣ ህንድ እና ቻይና “ባለሀብቶች” በጣም ርካሽ በሆነ የኪራይ ተመን  በሚስጥር ታድሏል (ይቅርታ ለ99 ዓመታት በኮንትራት ተከራይቷል)፡፡ አንድ የህንድ ኩባንያ “2,500 ካሬ ኪ/ሜ ስፋት ያለው ድንግል ለም መሬት – በእንግለዝ የዶርሴት ግዛትን የሚያህል” ከታክስ ነጻ በሚባል መልኩ በሳምንት 150 ፓውንድ (245 ዶላር) ሂሳብ ከኢትዮጵያ አገኘሁ በማለት ደስታውን እና ፈንጠዝያውን ገልጿል፡፡ (አዎ! እውነት ነው፡፡ ማንም እንደሚገምተው የብሩከሊን ግዛት ድልድይን በጣም ርካሽ በሆነ ዋጋ ለሽያጭ እንደማቅረብ ያህል ነው፡፡ ከዚያ ስምምነት ገዥው አካል ከፍተኛ የሚስጥር የሙስና ክፍያ ያገኛል፡፡ የገዥው አካል ተዋንያኖች ከሁሉም ባለሀብቶች እና ከሚሰጧቸው የግዥ ስምምነቶች ባለድርሻ አካላት ጋር ሚስጥራዊ (ድብቅ) ስምምነቶች አሏቸው፡፡

ዊንስተን ቸርችል በአንድ ወቅት “ሩሲያ በሚስጥር ውስጥ የተጠቀለለች ግራ አጋቢ እንቆቅልሽ ናት“ በማለት ተናግረው ነበር፡፡ እኔም በበኩሌ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል በሙስና ውስጥ የተጠቀለለ ግራ አጋቢ እንቆቅልሽ ነው ማለት እፈልጋለሁ፡፡ በሚስጥራዊ ስሜት ተጀቡኖ የሚገኘው ገዥው አካል በቅርቡ በሚያስገርም ሁኔታ በዓለም አቀፍ ደረጃ የማዕድን ኢዱስትሪ ዘንድ ተደራሽነት፣ ግልጽነት እና ተጠያቂነት እንዲሰፍን ጥረት ከሚያደርገው የአምራች ኢንዱስትሪዎች የግልጽነት ተነሳሽነት/Extractive Industries Transparency Initiative(EITI) ዘንድ አባል ለመሆን ጥያቄ አቅርቧል፡፡ ይህ ድርጊት ተኩላ የውስጥ የተንኮል ሚስጥሩን ደብቆ የበግ ለምድ በመልበስ ከበጎቹ መንጋ ጋር አባል ልሁን ብሎ ከጠየቀው ኢትዮጵያዊ ተረት ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡ ገዥው አካል ለEITI በበጎች ለምድ የተጠቀለለ የተኩላዎች እንቆቅልሽ ሊሆንበት አይችልምን?)

ሁሉንም የምንሰራውን ስራ ሁሉ ያውቃሉ

ባለፈው ሳምንት ሂዩማን ራይትስ ዎች የተባለው ዓለም አቀፋዊ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል በመጠነሰፊ የአሌክትሮኒክ የስለላ መርሀ ግብር ውስጥ ተዘፍቆ እንደሚገኝ ዘገባ አውጥቷል፡፡ ድርጅቱ “’የምንሰራውን ሁሉንም ነገር ያውቃሉ’ በኢትዮጵያ የቴሌኮሙኒኬሽን እና የኢንተርኔት ስለላ“ በሚል ርዕስ እንዲህ በማለት አጠቃልሏል፣ “የኢትዮጵያ መንግስት በኢትዮጵያ ውስጥ እና በውጭ የሚገኙ ተቃዋሚዎችን እና ጋዜጠኞችን ለመሰለል የውጭ ቴክኖሎጂን ይጠቀማል… መንግስት የሰላማዊ አመጸኞችን ድምጽ ጸጥ ለማድረግ የሀገሪቱን የቴሌኮሙኒኬሽን ሲስተምን በመሳሪያነት ይጠቀማል…፡፡“ ብሏል፡፡ የድርጅቱ ዘገባ እንደሚያመለክተው “የቴሌኮም ስርዓቱን ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሮታል…(ይህም በመሆኑ) የኢትዮጵያ የደህንነት ኃይሎች የሁሉንም የስልክ ተጠቃሚ ሰዎች የስልክ መረጃዎች ለማየት ያልተገደበ ስልጣን አላቸው፡፡“ ያለምንም የህግ አግባብ ወይም በዘፈቀደ ሁልጊዜ እና በቀላሉ የስልክ ጥሪዎችን ይመዘግባሉ፡፡ ከቤተሰብ እና ከጓደኛ የሚደወሉ ስልኮችን በተለይም የውጭ የስልክ ጥሪዎችን ትኩረት በመስጠት ይመዘግባሉ፡፡ ይህም የሚያገለግለው በፖለተካ አመለካከታቸው በአገር ውስጥ እንዳይንቀሳቀሱ ማዕቀብ የተጣለባቸው ድርጅቶች አባል ናቸው ብለው የሚጠረጥሯቸውን ግለሰቦች በዘፈቀደ በቁጥጥር ስር አውለው ህገወጥ ምርመራ ለማካሄድ ይጠቀሙባቸዋል፡፡”

ገዥው አካል “ድረገጾችን በመዝጋት እና ነጻ ወይም በኢትዮጵያ የፖለቲካ ሂደት ላይ ጠንካራ ትችት የሚያቀርቡትን ብሎገሮች (ተንታኞች)የመረጃ ፍሰትን ለመገደብ“ ረዥም ርቀትን ተጉዟል፡፡ ገዥው አካል “የተንቃሳቃሽ ስልክ መሰለል” እና በተደጋጋሚ የኦሮሞ ጎሳ አባላትን ዒላማ በማድረግ ስራ ላይ ተጠምዷል፡፡ በገዥው አካል ክልከላ የተጣለባቸው ድርጅቶች ለምሳሌም የኦሮሞ ነጻነት ግንባር አባል መሆናቸውን በግድ እንዲያምኑ ለማድረግ “በቴፕ የተቀዱ ድምጾችን በማሰማት በእስር ቤት የማሰቃያ ምርመራ ላይ ይጠቀሙባቸዋል፡፡“ የስለላ መመርመሪያ ቴክኖሎጂው የሚመጣው “እ.ኤ.አ ከ2006 እስከ 2009 ድረስ ብቸኛ የቴሌኮሙኒኬሽን አምራች ከሆነችው ከቻይና አገር ነው”፡፡ በርካታ “የአውሮፓ ካምፓኒዎችም የዲያስፖራ ማህበረሰብ አባላትን ዒላማ ለማድረግ የመጠቁ የስለላ ቴክኖሎጂ መሳሪያዎችን ለኢትዮጵያ ያቀብላሉ፡፡” ዘገባው በማያያዝም በኢትዮጵያ ላይ ህገወጥ ስለላ በማድረግ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣን በማፋጠን ረገድ ለዚህ ዕኩይ ምግባር አገልግሎት የሚውሉ ምርቶችን እና አገልግሎቶችን በሚያቀርቡ የአውሮፓ ድርጅቶች ላይ ጣቱን ቀስሯል፡፡

የገዥው አካል ታማኝ ሎሌ የሆኑት የኮሙኒኬሽን ሚኒስቴር ሚኒስትር የሆኑት አቶ ሬድዋን ሁሴን የተለመደውን አስልቺ ዝባዝንኪ ንግግር እንደበቀቀን በመድገም የሂዩማን ራይትስ ዎችን ስም እንዲህ በማለት ለማጠልሸት ሞክረዋል፡፡ “ሂዩማን ራይትስ ዎች በዘመቻ ሊስቶቹ ውስጥ ከያዛቸው ነገሮች  አንዱ የኢትዮያን ስም ማጠልሸት ነው፣ ስለሆነም ለዚህ ምላሽ መስጠት ምንም አስፈላጊነት የለውም፣ ምክንያቱም አዲስ ነገር የለውምና፡፡“ ብለዋል፡፡

ገዥው አካል ዕውነታውን በመገንዘብ ትክክለኛውን አቋም ለመያዝ ፍላጎት የለውም፡፡ በየጊዜው ዕውነታውን በመካድ የመቀበል ፍላጎት የሌለው በመሆኑ ስለዕውነታው ለመከራከር አቅም ያንሰዋል፣ ስለሆነም የሚወደውን እና የሚጠበቀውን ባለአምስት ጣት የህዝብ ግንኙነት ዘዴ ማለትም፡ 1ኛ) ዕውነታውን መካድ፣ 2ኛ) ዕውነታውን “ጥላሸት መቀባት” በሚል የሞኝ ፈሊጥ አፈር ድሜ ማብላት፣ 3ኛ) ዕውነታውን መደበቅ፣ 4ኛ) ከዕውነታው ለማራቅ የህዝብን ቀልብ ማስቀየስ፣ 5ኛ) የዕውነት አውጭዎችን እና ተናጋሪዎችን ስም ማጥፋት፡፡ ሆኖም ግን ዕውነታን መካድ እርባናቢስ ተግባር ነው፡፡

እ.ኤ.አ በ2010 አገር አቀፍ ምርጫ 99.6 በመቶ ውጤት አመጣሁ ብለው በቀን ብርሀን የዘረፉትን የህዝብ ድምጽ አስመልክቶ በቅርቡ ያረፉትን አቶ መለስ ዜናዊን የአውሮፓ ህብረት የምርጫ ታዛቢዎች ቡድን ከእውነታው ጋር ባፋጠጣቸው ጊዜ ሙልጭ አድርገው በመካድ እውነታውን አፈር ድሜ በማብላት “ይህ የቀረበው የምርጫ ዘገባ ቆሻሻ ማስቀመጫ ውስጥ መጣል ይኖርበታል” በማለት የህብረቱን የምርጫ ታዛቢ ቡድን አባላት ስም አጥፍተዋል፡፡ እ.ኤ.አ በኦገስት 2005 በሜይ በተካሄደው አገር አቀፍ ምርጫ አቶ መለስ ፓርቲያቸው መሸነፉን አስመልክተው በአውሮፓ ህብረት ፓርላሜንት አባል በማዳም አና ጎሜዝ እና በአባሎቻቸው ላይ ያላቸውን ጥላቻ በዘለፋ መልክ በማሳየት እንዲህ ብለዋል፣ “በሚቀጥሉት ቀናት እና ሳምንታት ይህንን ነጭ ውሸት ለማጋለጥ ምን እንደምናደርግ ታያላችሁ፣ እናም የዚህን ዘገባ የቆሻሻነት ባህሪያት ትመለከታላችሁ፡፡“

በሂዩማን ራይትስ ዎች የኢንተርኔት እና የቴሌኮሙኒኬሽን ስለላ ዘገባ መውጣት አስመልክቶ ገዥው አካል ተመሳሳይ አደንቋሪ ጩኸቱን በተለመደው መልኩ እንደበቀቀን ሲደጋግመው ተስተውሏል፡፡ ገዥው አካል በመካድ እራሱን ለመከላከል በሚል የሸፍጥ አካሄድ እንዲህ ብሏል፣ “የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ ለማጥፋት የተደረገ ጥላሸት የመቀባት ዘመቻ ነው፡፡“ እውነት ለመናገር “የፍራቻ እና ጥላሸት የመቀባት ዘመቻዎችን“ እና ነጭ ውሸቶችን በመቀፍቀፍ ረገድ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል ታላቁን የኬክ ድርሻ ይወስዳል፡፡  “የፍርሀት እና ጥላሸት የመቀባት ፖለቲካ በኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ ባቀረብኩት ትችቴ የገዥውን አካል ጥላሸት የመቀባት፣ ውሸቶችን የመፈብረክ እና በሙስሊም ማህበረሰብ አባላት የሀይማኖት ጉዳዮቻቸው የውስጥ ጣልቃገብነት ምክንያት ገዥው አካል ከድርጊቱ እንዲታቀብ በሰላማዊ መንገድ በመጠየቃቸው ብቻ የስም ማጥፋት ዘመቻውን አካሂዷል፡፡

የአስከፊይቷ ኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ሬፑብሊክ፣

እያንዳንዷ ቀን ባለፈች ቁጥር ኢትዮጵያ አስከፊና አማራሪ ቦታ አየሆነች ነው፡፡ አስከፊይቱ ኢትዮጵያ አስፈሪ አገር እየሆነች ነው፡፡ አገሪቷ ወሮበሎች የሚዘውሯት እየሆነች ነው፡፡ ሰብአዊ መብቶች የሚደፈጠጡባት አገር ነች፡፡ ስልጣኔ ወደኋላቀርነት የሚዘወርባት አገር ነች፡፡ ፍትህ የሚጣስባት፣ የዘር ማጥፋት የሚፈጸምባት፣ ህዝቦች የሚደኸዩባት እና የሚራቡባት፣ ወጣቶች አፋቸው የሚሸበቡባት፣ የሚለጎሙባት እና የሚታፈኑባት፣ የአካባቢ ተፈጥሮ ሀብት የሚወድምባት፣ ግድቦች ቋሚ ዝርያ ያላቸውን ህዝቦች መብት የሚገድቡባት እና ህዝቦች ወደ አስከፊ ሁኔታ እየወረዱ ያሉባት አገር ሆናለች፡፡ ጆርጅ ኦርዌል “በ1984” መፅፋቸው ላይ  እንዳሉት  ኢትዮጵያ የፌዴራል ሬፑብሊክ   2014  አስከፊ ሆናለች!

በኦርዌል “የ1984” ልብወለድ መፅፋቸው ስለ አንድ ጨቁአኝ መንግስት ፅፈዋል:: ይህም መንግስት በሁሉም ቦታ  ስለላ፣ ህዝብን የማሰቃየት እና አስተሳሰብን የመቆጣጠርና ፣ በገዥው አካል “የውስጣዊ ፓርቲ” ባለስልጣን ምሁራን ሰላማዊ አመጸኞችን እና የሀሳብ ነጸነትን “የሀሳብ ወንጀል” አድርገው ይጨቁኑ አንደነበር እና በማታለል በሚስጥራዊ ምርመራ እና በብዙህን ስነልቦናዊ ማሰቃየት ያደርግ ነበር:: ዋናው ቁንጮው አምባገነን “ታላቅ ወንድም” አየተባለ እንደ ትንሽ አምላክ የሚመለክ ነበር፡፡ ኦርዌል እንዲህ ሲሉ ጽፈዋል፣ “ማንም ቢሆን ‘ታላቅ ወንድምን’ አይቶ አያውቅም፡፡ በታላላቅ የምስል ማሳያ ሰሌዳዎች እና በርቀት የድምጽ መቅረጫዎች ነው ሊያየው የሚችለው፡፡ በእርግጠኝነት አልሞተም ይሆናል ብለን ልናምን እንችላለን፣ እናም በእርግጠኝነት መቸ ተወልዶ እንደነበር ጥርጣሪያዊ ግምት አለ፡፡ ታላቁ ወንድም የውሸት ውጫዊ ምስሉን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲያሳይ ፓርቲው የመረጠው ነው፡፡ የእርሱ ዋና ተግባር ለፍቅር፣ ለፍርሀት፣ እና ለበቀል፣ ስሜታዊነቱ ለድርጅቶች ሳይሆን ለግለሰቦች በማድረግ መስራት እንዲችል ነው፡፡” ደግሞም  “የታላቅ ወንድም” ፓርቲ መፈክሮች፡ “ጦርነት ሰላም ነው፣ ድንቁርና ሀይል ነው፣ ባርነት ነጻነት ነው” የሚሉ ሆነው ይገኛሉ፡፡

በ2014 በኢትዮጵያ ያለው “መንግስት” በእርግጠኝነት በኦርዌል ድርሰታዊ መንግስት ገጸ ባህሪያት ጋር አንድ ዓይነት ሆኖ ይገኛል፡፡ ታላቁ ወንድም አቶ መለስ ዜናዊ በህይወት ዘመናቸው ጊዜ በርቀት ምስል ማሳያ ሰሌዳ የማይበገሩ እና ኃያል ባለስልጣን መሪ ሆነው ነበር የሚታዩት እናም (ከህዝብ ጋር በመንገድ ላይ አይቀላቀሉም ነበር) እንዲሁም አሁን ደግሞ ከመቃብር፡፡ ለታላቁ ወንድም አቶ መለስ፣ “ሁሉም ስኬታማነት፣ ሁሉም ውጤታማነት፣ ሁሉም ድል፣ ሁሉም ሳይንሳዊ የምርምር ግኝት፣ ሁሉም ዓይነት ዕውቀት፣ ሁሉም ፍልስፍና፣ ሁሉም ክብር እና ሞገስ፣ ከእርሳቸው ቀጥተኛ አመራር እና ዝንባሌ የሚቀዱ የግል ሀብቶች ናቸው፡፡“ የእርሳቸው የፓርቲ እረዳቶች በሁሉም ቦታ የሚገኙት አቶ መለስ ዜናዊ የሁሉም እውቀቶች እና ፍልስፍናዎች ዋና ምንጭ ነበሩ፣ ናቸው፣ ወደፊትም ለዘላለም ሆነው ይኖራሉ፡፡ እርሳቸው የመልካም ነገሮች ሁሉ እና የታላቅ ሀሳቦች ምንጭ ናቸው፡፡

በአቶ መለስ እጅ ብድግ ተደርገው አሁን እርሳቸውን ተክተው የሚገኙት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በአቶ መለስ የቀብር ስነስርዓት ላይ በመገኘት እንዲህ የሚል ንግግር አድርገው ነበር፣ “የታላቁ እና የሁሉም ነገር ተምሳሌት የሆኑት መሪያችን እና “የታላቁን ባለራዕይ መሪ መንፈስ በመከተል ምን እንደምናስመዘግብ እና ወደፊትም ምን ማድረግ እንዳለብን መሰረቱን የጣሉልን“  መሪ ናቸው ብለዋል፡፡ ታላቁ ወንድም አቶ መለስ ኢትዮጵያን ከፍተኛ ወደ ሆነ ታላቅ እመርታ ለማድረስ ዕቅድ ያላቸው መሪ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ አቶ ኃይለማርያም አድናቆታቸውን በመቀጠልም እንዲህ ብለዋል፣ “ብልህ፣ የብሩህ አዕምሮ ባለቤት እና የኢህአዴግን ፓርቲ የመሰረቱ እንዲሁም የኢትዮጵያን የልማት ዕቅድ የነደፉ መሃንዲስ እና ቁርጠኛ መሪ ነበሩ“  አቶ ኃይለማርያም አክብሮታቸውን (አምልኮታቸው አላልኩም)  በማጠናከር አቶ መለስ የአገሪቱን ፖሊሲዎች እና ስትራቴጅዎች ዕቅድ የነደፉ እና ኢኮኖኖሚው በ10 በመቶ እና ከዚያም በላይ እድገት እንዲያስመዘግብ ላለፉት 9 ተከታታይ ዓመታት ጥረት ያደረጉ ናቸው በማለት ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ አቶ መለስ “የህዳሴው ቀያሽ እና ጀግና መሪ እንዲሁም የኢትዮጵያን የዕድገት እና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ያመነጩ ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት ከእኛ በአካል ቢለዩንም ራዕያቸው ከፓርቲያቸው ብቻ ሳይሆን በአገሪቱ ከሚገኝ/ከምትገኝ ከእያንዳንዱ/ዷ ዜጋ አዕምሮ ውስጥ ሰርጾ እንደሚኖር በአጽንኦ ተናግረዋል፡፡“

ታላቁ ወንድም አቶ መለስ በአንዳንድ ጥቂት የውጭ አገር ባለስልጣን ታናናሽ እህቶች አስተሳሰብ መሰረት ታናሹ አምላክ ካልሆኑ ቢያንስ “ታላቁ ሰው” ናቸው በማለት ዲስኩራቸውን አሰምተዋል፡፡ የእንግሊዝ የዓለም አቀፍ ልማት የቀድሞ የቶኒ ብሌር ጸሐፊ የነበሩት እና በአሁኑ ጊዜ ደግሞ የአምራች ኢንዱስትሪዎች የግልጽነት ተነሳሽነት/Extractive Industries Transparency Initiative ሊቀመንበር የሆኑት ማዳም ክላሬ ሾርት “በህይወቴ ካየኋቸው እጅግ በጣም ብሩህ የፖለቲካ ዕውቀት ካላቸው ሰዎች ሁሉ የበለጠ ነው” በማለት ለአቶ መለስ ያላቸውን ገደብየለሽ አድናቆት በመግለጽ አሞካሽተዋቸዋል፡፡ በተባበሩት መንግስታት የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደር የነበሩት እና በአሁኑ ጊዜ ደግሞ የኦባማ የብሄራዊ ደህንነት አማካሪ የሆኑት ማዳም ሱሳን ራይስ በተመሳሳይ መልኩ አድናቆታቸውን ገልጸዋል፡፡ በቀብር ስነ ስርዓቱ ላይ በመገኘት ባሰሙት የሀዘን መግለጫ ላይ እንዲህ ብለው ነበር፣ “እኔ የማውቃቸው አቶ መለስ በጣም ማራኪ ስብዕና ያላቸው ነበሩ፣ እናም ብዙውን ጊዜ ትክክለኛ ነበሩ…“ የኢትዮጵያው ታላቅ ወንድም አቶ መለስ እንደ ኦርዌል ድርሰት “ታላቁ ወንድም” በአሁኑ ጊዜ በህይወት ብቻ አይደለም በሩቅ ምስል ማሳያ ሰሌዳ እየቀረቡ ያሉት ሆኖም ግን “ጦርነት ሰላም ነው፣ ድንቁርና ኃይል ነው፣ ባርነት ነጻነት ነው” በማለት ታናናሾቻቸው ወንድሞቻቸውም እንዲተገብሩት ለመገፋፋት ከመቃብር ብቅ በማለት ጭምር እንጅ፡፡ ታናናሽ ወንድሞቻቸውን እንዲህ በማለት አስተምረዋል፣ “ስለላ የሚስጥር ነብስ ነው፡፡“

በእርግጥም በኢትዮጵያ ጦርነት ሰላም ነው (ሆኖም ግን ህዝቡ ወደ ታላቅ ቁጣ እና አመጽ እየተገፋ ቢሆንም ሁሉም ነገር ሰላም እንደሆነ አድርገው የማስመሰል ስራቸውን እያከናወኑ መሆናቸው ቀጥሏል፡፡) ድንቁርና ከፍተኛ ደስታ ነው (ሰዎች ጥቂት ባወቁ ቁጥር የበለጠ ደስተኛ እየሆኑ የመሄድ ሁኔታ እናም እውነቱን በማጣመም እና በማኮላሸት ህዝቡን ደንቆሮ አድርጎ ማቆየት) እና ባርነት ነጻነት ነው (“አምባገነኖች የሚያልሙት ነጻነት ሚስጥራዊነት ነው” ሲሉ ቢል ሞየርስ ተናግረዋል)፡፡

በነጻነት የማሰብ ነጻነት ለአምባገነኖቹ የግብአተ መሬት መግቢያ ምልክት ነው፡፡ ያልተሸበበው አዕምሮ ለድንቁርና አስፈሪ ነገር ነው፡፡ በኦርዌል ድርሰት 2+2=5 ነው፣ ምክንያቱም እያንዳንዱ/ዷ ሰው ይህን ተገድዶ/ዳ እንዲቀበል/እንድትቀበል ጫና ስለሚጣልበት/ባት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ያለው 6.5% የኢኮኖሚ ዕድገት ከ11-15% ካለው የኢኮኖሚ ዕድገት ጋር እኩል ነው፣ማንም የሚያምንበት እስካገኙ ድረስ (ያ ማለት ከዓለም ባንክ እና ከዓለም አቀፉ የፋይናንስ ድርጅት በስተቀር)፡፡ የኦርዌል የ1984 ድርሰት የመፈክር ቀመር በኢትዮጵያ 2014 እንዲህ በሚል ታድሷል፡ ድህነት ብልጽግና ነው፣ ረኃብ ጥጋብ ነው፣ የመንግስት ዕኩይ ምግባሮች ወይም ስህተቶች ሰብአዊ መብቶች ናቸው፣ ጭቆና እና የዴሞክራሲ እጦት የዴሞክራሲ መንበሽበሽ መገለጫ ነው፣ ድንቁርና ምሁርነት ነው፣ በኢትዮጵያ ድንቁርና የብሄራዊ ድንቁርና አንድ የመሆን ፍትሀዊነት ነው፡፡ የመንግስት ዋና ዓላማ ለማጣመም፣ እውነታውን ለመለጠጥ እና በማሸት ድንቁርናን፣ አፈ ልጉምነትን እና ያለመጠየቅ ሁኔታዎች በአሉበት እንዲቆዩ ለማድረግ ነው፡፡

ኔልሰን ማንዴላ እንዲህ ብለው ነበር፣ “ትምህርት ዓለምን ለመለወጥ የምንጠቀምበት ጠንካራ መሳሪያ ነው“፡፡ እውቀት፣ መረጃ፣ ንቃተ ህሊና እና ምሁርነት በ21ኛው ክፍለ ዘመን በወንዶች እና በሴቶች እጅ የሚገኙ የእራሳቸውን፣ የቤተሰቦቻቸውን እና የአካባቢውን ማህበረሰብ ህይወት ለመለወጥ፣ እንዲሁም የየሀገሮቻቸውን ዕጣ ፈንታ ለመወሰን በጣም ጠቃሚ የሆኑ መሳሪያዎች ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ላለው ገዥ አካል ተቃራኒው በትክክል ይመጥነዋል፡ ድንቁርና እና ሚስጥራዊነት በስልጣን ላይ እንደ መዥገር ተጣብቆ ለመቆየት እና ለውጥ እንዳይመጣ ለመከላከያነት በጣም ጠንካራ የሆኑ መሳሪያዎች ናቸው፡፡ “የአስከፊይቷ ኢትዮጵያ ታናናሾቹ ወንድሞች” ብቸኛው ዓላማ “ሚስጥራዊነት ኃይል ነው፣ ሚስጥራዊነት ጥንካሬ ነው”፡፡ ሚስጥራዊነት ከድንቁርና ጋር ሲቀላቀል ፍጹም የሆነ ስልጣንን ይሰጣል፡፡ በአውቆ ደንቆሮዎች (ፈልገው ደንቆሮ የሆኑ) እጅ ያለ ስልጣን ብዙሀኑን ለማሰቃየት፣ ለማዳከም እና ወኔ የለሽ ለማድረግ ማረጋገጫ ይሰጣል፡፡ “ማደንቆር፣ ማደህየት፣ እና መከፋፈል ቆሻሻን እንደማስወገጃ የሚያገለግሉ የጫማ ብሩሾች” የመሳሰሉት “ለውስጣዊ የፓርቲ” (በኢትዮጵያ በመንግስት ውስጥ መንግስት) በመሆን የሚያገለግሉ አዚሞች ናቸው፡፡

በተለያዩ አጋጣሚዎች ሳቀርበው እንደነበረው የመከራከሪያ ጭብጥ ገዥው አካል በአብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ ዘንድ የተጠላ እና በንቀት የሚታይ አምባገነን ፍጡር ነው፡፡ ስለሆም እንቅልፍ የለሽ ሌሊቶችን ያሳልፋል፡፡ ትንሽ የአዕምሮ ሰላም ለማግኘት ጥረት አድርገዋል፣ ሆኖም ሰላሙን ለማምጣት ባይችሉም፡፡ የአንዱን ጎሳ አባላት በሌላው ላይ ለማስነሳት በማለም ማቋረጫ የሌለው የጥላቻ የፕሮፖጋንዳ ዘመቻዎችን ያካሂዳል፡፡ በሙስሊሙ ማህበረሰብ እና በክርስትና እምነት ተከታይ ወገኖቻችን ዘንድ ጦርነት እንዲነሳ ለማድረግ ሌት ከቀን ተንቀሳቅሷል፡፡ እናም አምላክ ምስጋና ይግባው እና ይህ ዲያብሎሳዊ እኩይ ምግባሩ ሁሉ ሙሉ በሙሉ ከሽፈውበታል! ተጽዕኖ ሊፈጥሩ የሚችሉ የማያቋርጥ ፕሮፓጋንዳ፣ የተሳሳተ መረጃ መስጠት፣ ሆን ብሎ የውሸት መረጃ መስጠት፣ ሌሎችን ሰላማዊ ሰዎች የዕኩይ ምግባሩ ደጋፊ እንዲሆኑ ማጥመቅ፣ ያለፉትን ዘመናት የበከቱ መፈክሮች እና ያፈጁ ያረጁ የማይለወጡ የመከኑ ቀኖናዎችን በማንገብ በስልጣን ላይ እንደ መዥግር ተጣብቆ ለመኖር ያለ የሌለ የሞት ሽረት ትግል ማድረግ የሚሉት ናቸው፡፡ በተጨባጭ የሚታዩ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎችን በሸፍጥ በተሞላ የሀሰት አሃዛዊ መረጃ በማቅረብ የኢኮኖሚ እድገት እና ልማት አለ ለማለት በውሸት ካባ አሽሞንሙነው ያቀርባሉ፡፡

ላለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ያህል አቶ መለስ እና ወሮበላ ሎሌዎቻቸው ኢትዮያውያንን/ትን በድንቁርና ዘፍቀው ሀሴት በማድረግ ለማቆየት ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡ በዜጎች ላይ የጠብመንጃ አፈሙዝ ደግነው ህዝቡ በግድ ምንም ጭራቃዊነት ድርጊት የለም የሚል ምስክርነት እንዲሰጥ፣ እኩይ ተግባራት የሉም ብሎ እንዲናገር፣ ምንም ጭራቃዊ ተግባራት አላየሁም አልሰማሁም ብሎ እንዲመሰክር ሲያስገድዱት ቆይተዋል፡፡ አቶ መለስ እና የዕኩይ ምግባር ተባባሪዎቻቸው ዓለም አቀፍ የሬዲዮ ሞገዶች እና የሳቴላይት ስርጭቶች ለህዝብ እንዳይደርሱ ለማድረግ እና ለማፈን እጅግ ብዙ ገንዘብ አውጥተዋል፡፡ የወሳኝ መረጃዎች እና ሀሳቦች አማራጭ የመረጃ ምንጭ የሆኑትን የኢንተርኔት አገልግሎት አግደዋል፡፡ ፍሪደም ሀውስ የተባለው ድርጅት እ.ኤ.አ በ2012 ባወጣው ዘገባ መሰረት እ.ኤ.አ በ1941 የተቋቋመው እና በዓለም ላይ በጣም የተከበረው መንግስታዊ ያልሆነ የምርምር እና የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት “ኢትዮጵያ በኢንተርኔት እና በተንቀሳቃሽ ስልክ አጠቃቃም ከዓለም በመጨረሻው ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ገልጿል፡፡ አገልግሎቱ ዝቅተኛ ሽፋን ቢኖረውም በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ በዚሁ ላይ የማያላውስ የቁጥጥር ስርዓት በመዘርጋት የኢንተርኔት ስለላ ዕኩይ ምግባርን በአገር አቀፍ ደረጃ በመተግበር እና የእራሱን ዜጎች ሰብአዊ መብት በመደፈጥጥ ከሰሃራ በታች ካሉ የአፍሪካ አገሮች ብቸኛው አምባገነን መንግስት ሆኗል፡፡” መንግስት ነጻውን ፕሬስ ይዘጋል፣ የመረጃ ዘጋቢዎችን ያስራል፣ እንዲሁም የእራሱን አስደንጋጭ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣ ወንጀሎችን የተንሰራፋውን አስፈሪ ሙስና የሚያጋልጡትን አታሚዎችን እና የብሎገሮች ባለሙያዎችን ያስራል፡፡ መንግስት “የዕድገት እና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ” እያለ የሚጠራው ብዙ የተደሰኮረለት ዕቅድ “ኢትዮጵያን ከ13 ወራት ጸሐያማ ብርሀንነት ወደ ድንቁርና እና ወደማያቋርጥ የጨለማ የኑሮ አዘቅት ውስጥ እያሸጋገራት ይገኛል፡፡”

በገዥው አካል እየተከናወኑ ያሉት ሁሉም የምርመራ እና የስለላ ፕሮግራሞች ማጠንጠኛ ዓላማ “ኢትዮጵያ የተዋረደች ግዛት” ሆና ደንቆሮ ንጉሶች፣ ንግስቶች ልዑሎች እና ልዕልቶች የሚገዟት እንድትሆን በስፋት የታቀደ ሸፍጥ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ያለው የትምህርት ስርዓት በሙስና የተዘፈቀ እና ገዥው አካል ለያዘው ዕኩይ ዓላማ ድጋፍ እንዲያገኝ ዜጎችን በግድ ያለውድ አባል እንዲሆኑ የማጥመቂያ መሳሪያ ነው፡፡ ገዥው አካል ለወጣቱ ደረጃውን ያልጠበቀ ጥራት የሌለው ትምህርት በማቅረብ እና ከዘመኑ ጋር የሚሄዱ የመማሪያ ዕድሎችን በመንፈግ ለዘላለም ወጣቱን የእውቀት ሽባ አድርጎ ማስቀመጥ ብቻ አይደለም ዓላማው ሆኖም ግን ወጣቱ በኢንተርኔት አጋዥነት ህይወቱን ለመለወጥ የሚያስችለውን ዕውቀት እንዳይሸምት እና የሀገሩን መጻኢ ዕድል እንዳይወስን ለማድረግ የተሸረበ እኩይ ምግባር ጭምር እንጅ፡፡

እ.ኤ.አ በሴፕቴምበር 2010 “አገር አቀፍ ማጥመቅ” በሚል ርዕስ ባቀረብኩት ትችት ትምህርትን ለፖለቲካ ጥቅም እያዋለ ባለው የአቶ መለስ አገዛዝ ላይ የሰላ ተችት አቅርቢያለሁ፡፡ “የትምህርት ሚኒስቴር” ከጥቂት ዓመታት በፊት ያወጣው የርቀት ትምህርትን ህጋዊ ያለመሆን (የትምህርት ፕሮግራሞች በተለመደው መልክ በዩኒቨርስቲ ግቢዎች የመማሪያ ክፍሎችን በመጠቀም ካልሆነ በስተቀር) በሚል በአገር አቀፍ ደረጃ የተላለፈው የዕግድ መመሪያ (የኦርዌል አንዱ የሆነውን “የዕውነት ሚኒስቴር” (ድንቁርና)  እንዳስታውስ አደረገኝ፡፡ በሚያስገርም ሁኔታ አቶ መለስ እና ቁንጮ የጦር አበጋዞቻቸው “የድህረ ምረቃ ትምህርታቸውን” የተከታተሉት በውጭ አገር የርቀት ትምህርት ፕሮግራም አማካይነት ነው፡፡) ገዥው አካል የህግ እና የትምህርት ሙያዎችን በመንግስት ቁጥጥር ስር ባሉት ዩኒቨርስቲዎች ብቻ እንዲሰጡ በማወጅ የፓርቲ ዕጩ አባላትን በመቀፍቀፍ የትምህርት እና የህግ ሙያዎችን በጅምላ ጠቅልሎ ለመያዝ የታለመ መሰሪ ተግባር እንደሆነ ገልጫለሁ፡፡ በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት የአካዳሚክ ነጻነት የለም፡፡ እ.ኤ.አ በፌብሯሪ 2008 “አምባገነንነት በአካዳሚው ማህበረሰብ ውስጥ“ በሚል ርዕስ በመቀሌ ዩኒቨርስቲ የህግ ትምህርት ቤት ውሰጥ የአካዳሚክ ነጻነት እጦት በሚል ርዕስ ትኩረትን የሳበ ትችት አቅርቤ ነበር፡፡

ገዥው አካል ህዝቡን የሚሰልለው ለምንድን ነው? 

ገዥው አካል ህዝቡን በሚስጥር ይሰልላል ምክንያቱም ህዝቡን ስለሚፈራው ነው፡፡ እ.ኤ.አ በ1962 ፕሬዚዳንት ጆን ኬኔዲ ለአሜሪካ ህዝብ እንዲህ የሚል ሀሳብ አቀረቡ፣ “ደስ የማይሉ እውነታዎችን፣ የውጨ ሀሳቦችን፣ ባዕድ ፍልስፍናዎችን እና ተወዳዳሪነት ያላቸውን እሴቶች ለአሜሪካ ህዝብ ኃላፊነት ለመስጠት አንፈራም፡፡ ለአንድ አገር ህዝቡ እውነታውን እና ሀሰቱን በግልጽ አደባባይ እንዲዳኝ የማይሰጥ መንግስት የእራሱን ህዝብ የሚፈራ ብቻ ነው፡፡“ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል ህዝቡን ይፈራል፣ እናም የተጠናወተውን የፍርሀት በሽታ ለማስወገድ ሲል ህዝቡን በሚስጥራዊ የምርመራ ፕሮግራሞች መሰለል እና ማስፈራራትን እንደመፍትሄ ወስዶ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡

በጣም በአሳዛኝ ሁኔታ የሚያስገርመው እውነታ ግን በአሁኑ ጊዜ አንደሃእማኖት የያዘው ሚስጥራውነት በህገመንግስቱ ላይ ያለውን የመረረ ጥላቻ ያመላክታል፡፡ በአንቀጽ 12 (1) ስር “የመንግስት ተግባራት እና ተጠያቂነት“ በሚል የተጠቀሰው የኢትዮጵያ ህገመንግስት መንግስትን ለግልጽነት እና ተጠያቂነት ኃላፊነት እንዳለበት በግልጽ አስቀምጦታል፡፡ እንዲህም ይላል፣ “መንግስት የሚያከናውናቸው ተግባራት ሁሉ ግልጽነት ባለው ሁኔታ በይፋ ለህዝብ ግልጽ ይደረጋሉ፡፡“ ገዥው አካል ይህንን ህገመንግስታዊ ድንጋጌ በተቃራነው ወስዶ “የመንግስት እንቅስቃሴ በአጠቃላይ ሚስጥራዊ እና ለህዝቡ ግልጽነት በጎደለው ሁኔታ ተግባራዊ ይደረጋል የሚል ትርጉም በመስጠት በዚሁ መሰረት ትኩረት ሰጥቶ እየፈጸመው ይገኛል፡፡“ ሚስጥራዊነት ህዝቡን ለማታለል ጠንካራ መሳሪያ ነው፡፡

ታላቁ የፈረንሳይ የስነጽሁፍ ሰው ቪክቶር ሁጎ እንዲህ ብለው ነበር፣ “ወራሪን ጠላት መቋቋም ይቻላል፣ ጊዜው የደረሰ ሀሳብን ግን በፍጹም መቋቋም አይቻልም፡፡“ የኢንተርኔት አገልግሎት ጊዜው የደረሰ ሀሳብ ነው፡፡ ከኢንተርኔት በፊት የነበረው ጊዜ ተመልሶ አይመጣም፣ ከኢንተርኔት በኋላ ያለው ጊዜ ብቻ ነው ያለው፡፡ ድንቁርና ሳይሆን ኢንተርኔት በዓለም ላይ ታላቅ እኩልነትን የሚያመጣ እና ዴሞክራሲን የሚያጎለብት ሁነኛ መሳሪያ ነው፡፡ ውድ ያልሆነ የግል ኮምፒውተር ወይም ተንቀሳቃሽ ስልክ በመጠቀም በማንኛውም ቋንቋ በአንድ ጊዜ ለአንድ ሰው እውቀት እና መረጃ በእጅ ጣቶች ላይ የሚገኙ ሀብቶች ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል በማይታየው የሀሳብ እና የእውቀት ግዛት ላይ ከፍተኛ ጦርነትን በማካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ ኢንተርኔት የ21ኛው ክፍለ ዘመን ምንጊዜም ቢሆን በማይጠወልገው አረንጓዴ ልምላሜን በተላበሰው የጥሩ እና መጥፎ የውቀት ዛፍ (እፀ በለስ) መፃፍ ቅዱስ ላይ አንዳለው ይመሰላል፡፡ ገዥው አካል በእራሱ መለኮታዊ ስልጣን በኢትዮጵያ ላይ እንዲህ የሚል ገደብን ሊያውጅ ይፈልጋል፣ “ከጥሩ እና መጥፎ የእውቀት ዛፍ እፀ በለስ ላይ መብላት የለባችሁም፣ ከዚያ የምትበሉ ከሆነ በእርግጠኝነት ትሞታላችሁ፡፡“ የኢንተርኔት “የዛፍ እውቀት” የሙት መንፈስ ለሆኑት ደንቆሮ አምባገነኖችም የህይወት እስትንፋስ ይሰጣል፡፡ የኢንተርኔት ጂኒ ከጠርሙሱ ውጭ ነው፣ እናም እርሱን መልሶ ወደ ጠርሙሱ ለማስገባት ፈጽሞ አይቻልም፡፡ እንደዚሁም ሁሉ የቴሌኮም ምርመራ፣ የኤሌክትሮኒክ ፍተሻ ወይም ደግሞ ጠቅላላ የተሌሌኮሙኒኬሽን ስርዓቱን በሞኖፖል በቁጥጥር ስር ማዋል በምንም ዓይነት መልኩ “የሳይበር ተዋጊዎችን”  በእውነት፣ በእውቀት እና በመረጃ እራሳቸውን ከማጠናከር ለአፍታም ቢሆን አይገታቸውም፡፡ በኢንተርኔት ዘመን ለእውነት፣ ለእውቀት እና ለመረጃ መስፍን ተገዳዳሪ ሆኖ መቅረብ ፍጹም እርባናየለሽ ተግባር ነው!

ደህና፣ “ታላቁ ወንድም” አቶ መለስ ዜናዊ ላይመለሱ ከኢትዮጵያ ወደ ዘላለማዊው ዓለም ሄደዋል፣ ሆኖም ግን “በእርቀት የምስል ማሳያ የኤሌክትሮኖክ ሰሌዳ” ላይ ብቅ እያሉ እና በመቃብራቸው ውስጥ በመንፈስ ሆነው “ታናናሽ ወንድሞቻቸውን” ማለትም “የውስጣዊ ፓርቲ” አባላትን በማዘዝና በማገልገል ላይ ይገኛሉ፡፡ አሁንም ራዕያቸውን ያልማሉ፣ ያስተውላሉ፣ ይመለከታሉ፣ ያጮልቃሉ፣ አተኩረው ያያሉ፣ የስለላ ተግባራትን ያካሂዳሉ፣ ለብዙ ጊዜ አፍጥጠው ይመለከታሉ፣ ያዳምጣሉ፣ ያነፈንፋሉ፣ እናም ድምጻቸውን ከፍ አድርገው አደንቋሪ መዝሙራቸውን ይዘምራሉ፣ እንዲህ እያሉ፣

… ፓርቲው በአጠቃላይ ለእራሱ ሲል ስልጣንን ጠቅልሎ መያዝ አለበት፡፡ ለሌሎች ደግነት ደንታ የለንም፣ እኛ ፍላጎታችን ከስልጣናችን ንጹህ ስልጣን ላይ ተንጠልጥለን መቆየት ብቻ ነው፡፡ ንጹህ ስልጣን ማለት በአሁኑ ጊዜ ምን ማለት እንደሆነ ትገነዘባላችሁ የሚል እምነት አለን፡፡ እኛ ምን እንደምናደርግ ስለምናውቅ ከአለፉት ንጉሳዊ አገዛዞች እንለያለን፡፡ ሌሎቹ በሙሉ እኛን የሚመስሉት አንኳን ፈሪዎች እና አስመሳዮች ነበሩ፡፡ የጀርመን ናዚዎች እና የሩሲያ ኮሙኒስቶች በአሰራር ዘዲያቸው እኛን ይመስላሉ፣ ሆኖም ግን የእራሳቸውን ፍላጎት ለመገንዘብ ድፍረቱ አልነበራቸውም፡፡ ያስመስሉ ነበር፣ ምናልባትም ስልጣንን ከፈቃድ ውጭ እና ለተወሰነ ጊዜ በመያዝ ማስመሰያነት እያቀረቡ የሰው ልጆች በምድረ ገነት በነጻ እና በእኩልነት ይኖራሉ እያሉ ከንቱ ስብከት ይሰብኩ ነበር፡፡ እኛ እንደ እነርሱ አይደለንም፡፡ ማንም እስከ አሁን ስልጣን ይዞ በራሱ ፈቃድ ስልጣኑን አሳልፎ እንደማይሰጥ እናውቃለን፡፡ ስልጣን በእራሱ መንገድ አይደለም፣ ግብም አይደለም፡፡ ማንም አብዮትን ለመጠበቅ ሲል አምባገነንነትን አይመሰርትም፡፡ የማሰቃየት ዓላማው ማሰቃየት ነው፡፡ አሁን ግንዛቤ ማግኘት እንደጀመራችሁ ይገባኛል፡፡

የኢትዮጵያ የውስጥ ፓርቲ ስለ21ኛው ክፍለ ዘመን ጥቂት እውነታዎችን መገንዘብ ይኖርባቸዋል፡ ሚስጥራዊነት ደካማነት ነው፣ ድንቁርና ደደብነት ነው፡፡ ነጻነት የሰው ልጅ ውስጣዊ ባህሪ መገለጫ ነው፣ እናም እውነት እነሱን እና ኢትዮጵያውያንን/ትን በሙሉ ነጻ ታወጣለች፡፡

ኦርዌል እንዲህ በማለት ጽፈው ነበር፣ “ሸፍጥ በተንሰራፋበት ስርዓት ውስጥ እውነትን መናገር አብዮታዊ ድርጊት እንደመፈጸም ያህል ይቆጠራል፡፡ ሆኖም ግን ጸጥ ማለት እንደ አብዮታዊ ድርጊት ቅቡል በሚሆንበት ጊዜ ምን ማድረግ ይቻላል?“

“በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ምሁራን፣ አካዳሚክስ፣ ፕሮፌሰሮች እና የተማረው ልሂቅ ትውልድ የደንቆሮዎችን አምባገነንነት በተጨባጭ ተግባራት በምስክርነት እየተመለከተ እንደ ድንጋይ ሀውልት ተገትሮ ጸጥ ካለ በእያንዳንዷ ጉዳይ ላይ ድምጽ ለሌላቸው ድምጽ የሚሆኑ ዜጎች  ኃላፊነት በጥቂቶች ላይ ብቻ የሚወድቅ በመሆን ሸክሙ የበዛ ይሆናል፡፡” “የትምህርት ሙስና እና ኢትዮጵያን ማደንቆር“ ከሚለው ቀደም ሲል ካቀረብኩት ትችቴ የተወሰደ ነው፡፡

እንኳን ወደ አስከፊዋ የፌዴራል ሬፑብሊክ ኢትዮጵያ በሰላም መጣችሁ!

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

መጋቢት 23 ቀን 2006 .