እውነተኛው አ.ኢ.ግ.ተ. (EITI) ወይስ የማዳም ክላሬ የሙስና ማጋበሻ ቡድን?

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

Deception 3 ማዳም ክላሬ አሸንፈዋል! እንኳን ደስ ያለዎት፣ ማዳም ክላሬ!

 

ባለፈው ሳምንት የ “አምራች ኢንዱስትሪዎች የግልጽነት ተነሳሽነት/Extractive Industries Transparency Initiative (EITI) ሊቀ መንበር የሆኑት ማዳም ክላሬ ሾርት ስልጣናቸውን ከህግ አግባብ ውጭ በመጠቀም እና በማስፈራራት በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል የሙስና ማጋበሻ ቡድናቸው አባል እንዲሆን ለማስቻል የEITI የቦርድ አባላት ድምጻቸውን እንዲሰጡ በማድረጉ ጥረት ሲያካሂዱት የቆዩት ዥዋዥዌ ጨዋታ ተሳክቶላቸዋል፡፡ ማዳሟ አሮጌውን እና ያረጀ ያፈጀውን የአሰራር ሂደትን ማለትም እጅ በመጠምዘዝ፣ በኃይል በማስፈራራት፣ ስልጣንን ከህግ አግባብ ውጭ በመጠቀም በማስገደድ፣ ከኋላ ሆኖ በማስተኮስ፣ ስልጣንን መከታ በማድረግ ከህግ አግባብ ውጭ በግድ እንዲያምኑ በማድረግ፣ አሰልች እና የምጸት ቃላትን በመጠቀም እና የህጻናት ዓይነት እሽሩሩ ዘይቤ ቁጣን በመከተል ለርካሽ ጥቅም ሲባል የሞት ሽረት ትግል በማድረግ ሀቅን በመደፍጠጥ በሸፍጥ ለጊዜውም ቢሆን ሀሳባቸውን አሳክተዋል፡፡ ማዳሟ በእንደዚህ ዓይነት እኩይ ምግባራቸው የተካኑ ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ በ2003 እንግሊዝ እና አሜሪካ በኢራቅ ላይ ወረራ ለማካሄድ በተዘጋጁበት ጊዜ ማዳም ሾርት በቶኒ ብሌር ላይ ጠንካራ የሆነ ትችት በማቅረብ ከመንግስታቸው ዓለም አቀፍ የልማት ጸሐፊነት ስልጣናቸውን በገዛ ፈቃዳቸው እንደሚለቁ በማስፈራራት ሁኔታውን በመቃወም የኃይል ትችት አቅርበው ነበር::   ብሌርንና የአሜሪካን መንግስት ሲተቹ አንዳሉት “ሆኖም ግን በዚያም ተባለ በዚህ የጦርነቱ መካሄድ አይቀሬነት በተረጋገጠበት ወቅት፣ ሌሎችን አገሮች በኃይል እና በማስፈራራት ለጦርነቱ መካሄድ ድጋፍ እንዲሰጡ ያስገድዱ ነበር፡፡“

አንደ ኢራቁም ጉዳይ: ማዳም ክላሬ “በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል ድምጽ በማግኘት የEITI አባል እንዲሆን ከህግ አግባብ ውጭ ስልጣንዎን በመጠቀም  የቦርድ አባላትዎን ያስገድዱ እና ያሳምኑ እንደነበር እናውቃለን፡፡“ እንኳን ደስ ያለዎት! ድል ተቀዳጅተዋል፡፡ የድል ደረጃ አድርገው ይውሰዱት፣ ጣራውን ከፍ ያድርጉት፡፡ “ለሰብአዊ መብት የሚሟገቱትን ድል አድርገዋል፣ በእራስዎ ቦርድ ያሉትን የሲቪል ማህበረሰብ ተወካዮችን በመላው ዓለም ፊት አዋርደዋል፣ እናም ዕድለቢሶችን እና ድምጽ አልባ የኢትዮጵያ ዲያስፖራ ማህበረሰብ አባላትን አባርረዋል፣ “መብቶቻቸውንም” ደፍጥጠዋል፣ አሁን አዲስ አበባ በመሄድ የስኬት በዓልዎን ቸበርቻቻ ማክበር ነው፡፡ በትግል ያገኙት ውጤት ነውና፡፡ ቻምፓኝ እና ኮኛክ እንደ ጅረት ውኃ ይፍሰስ፡፡ አሁን EITIን የእርስዎ የግል ንብረት አድርገውታል፡፡ የእራስዎ ህጻን ነው! ለ EITI አዲስ ስም ያውጡለት፡፡ የማዳም ክላሬ የሙስና ማጋበሻ ድርጅት በሉት? ጥሩ የእምነተቢሶች የመጠሪያ ስምን ይዟል፡፡

በጣም የሚያስደንቀው እውነታ ግን የማዳም ሾርት ፍልስፍና (እራሳቸው “መርህ” እያሉ የሚጠሩት) በብዙ በሙስና በተዘፈቁ አገሮች የማዕድን እና አምራች ኢንዱስትሪዎች ዘርፍ ላይ ዕዉን እየሆነ መጥቷል፡፡ በኢትዮጵያ ያለውን ገዥ አካል የEITI አባል በማድረጉ እረገድ ማዳም ሾርት የማዕድን ሙስናን ለመቆጣጠር የሚያስችል ቀላል እና በሚከተለው ዳህራ ላይ ትኩረት ያደረገ በአጭር ርቀት ላይ የተመሰረተ ድሁር ህልዮት ቀምረዋል፤ ህልዮቱም እንዲህ ይላል፣ “በዓለም ላይ በጣም በሙስና የተዘፈቁ ገዥ አካላት የይስሙላ የግልጽነት እና ተጠያቂነት ካባን ደርበው የEITI አባል እንዲሆኑ መፍቀድ፡፡“ ከዚያም እግሮችን በማንሸራተት መደነስ እና ማቀንቀን፡፡ ስለግልጽነት እና መልካም አስተዳደር ጥቂት አስመሳይ ቃላትን እና ሀረጎችን በማነብነብ የህዝብ እምነትን ለማግኘት የማታለያ ጥረት ማድረግ፡፡ የውሸት በእመኑኝ ላይ የተመሰረቱ ጥሩ የሚመስሉ የቢሮክራሲ ፍሬ ከርስኪ የታጨቁበት የማመልከቻ ቅጽ መሙላት፡፡ ከዚያም በማዕድን ዘርፍ ስራው ጥሩ ተሞክሮ እና ታማኝ መሆናቸውን በመግለጽ የአባልነት ጥያቄውን የምስክር ወረቀት ለማግኘት መጠየቅ፡፡ በመጨረሻም ከደስታ የመጨረሻው ከፍተኛ እርከን ላይ በመድረስ ሰርግ እና ምላሽ ማድረግ ትልቁ ግባቸው ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ ማዳም ክላሬ ሾርት ገዥውን አካል የጸረ ሙስና ተዋጊ ጦር አስመስሎ በማቅረብ እንዲሁም ወሮበላ ዘራፊዎችን እና ሸፍጠኛ ወንጀለኞችን በእራሳቸው ተለክቶ የተሰፋ የማስመሰያ ካባ በማልበስ በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ፊት የተከበሩ የአገር መሪዎች አስመስሎ ለማሳየት እና ለቀጣዮቹ ሶስት ዓመታት ያለምንም እንከን የጥሩዎች ሁሉ ተምሳሌት አድርጎ ለማቅረብ የተቀመረ ስሌት ነው፡፡ እንግዲህ በዚህ መንገድ ነው በአፍሪካ እና በሌሎች አገሮች ያለው በሙስና የበከተው የማዕድን እና የተፈጥሮ ጋዝ ዘርፍ በማዳም ክላሬ ሾርት ከሙስና የማጽዳት የአሰራር ዘይቤ የተቃኘው፡፡

በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል የEITI አባል እንዲሆን የተሰጠው ውሳኔ ፍጹም በሆነ ሙስና የተደረገ እና የማስመሰያ የአባልነት ተውኔት ነው፡፡ እ.ኤ.አ በ2010 ገዥው አካል ለአባልነት ያቀረበው ጥያቄ ውድቅ በተደረገበት ጊዜ የተሰጠው ምክንያት:- “የኢትዮጵያ የበጎ አድራጎት እና ማህበራት አዋጅ’ የሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች በነጻነት እንዳይንቀሳቀሱ በሂደትም ትርጉም ያለው ተሳትፎ እንዳያደርጉ ደንቃራ ሆኗል ወደፊትም ይሆናል፤ ስለሆነም የበጎአድራጎትእናማህበራትአዋጅእስካልተወገደድረስኢትዮጵያEITI አባልእንድትሆንእንደማይወስን በተጨባጭ ገልጾ ነበር፡፡ በ EITI ታሪክ በእንደዚህ ያለ የአፋኝነት ህግ መሰረት ከሰብአዊ መብት አጠባበቅ ጋር በተያያዘ መልኩ አንዲት አገር የድርጅቱ አባል እንዳትሆን የአባልነት ጥያቄው ውድቅ ሲደረግ የመጀመሪያው እና ብቸኛው ክስተት ነው፡፡ (የተሰመረው አጽንኦ ለመስጠት ነው)፡፡

ታዲያ ኢትዮጵያን በአሁኑ ጊዜ በአባልነት ለመቀበል የተቻለው በስራ ላይ እየተተገበረ ያለው “የበጎ አድራጎት እና ማህበራት አዋጅ” ተለውጦ ነው? እ.ኤ.ኤ ከ2010 ጀምሮ በኢትዮጵያ የሲቪል ማህበረሰብ እንቅስቃሴ ላይ ምን የተለወጠ ነገር አለ? “በአዋጁ” መውጣት እና በስራ ላይ መዋል ቀጥተኛ እንደምታ ምክንያት እ.ኤ.አ በ2010 ብዛታቸው 4,600 የነበሩት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በአስደንጋጭ ሁኔታ ቁጥራቸው አሽቆልቁሎ በሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ በዓመቱ መጀመሪያ አካባቢ 1,400 ሊሆኑ  ችለዋል፡፡ “ከእነዚሁ ከተረፉት እና በሞት የሽረት ትግል ውስጥ በመንፈራገጥ ላይ ከሚገኙት ድርጅቶች ውስጥ ደግሞ በአዋጁ አሳሪነት ምክንያት 90 በመቶ ወይም ከዚያ በላይ የሚሆነውን የሰው ኃይላቸውን እንዲቀንሱ ተገደዋል፡፡”

በሶስት ወራት ውስጥ በአንድ ጊዜ እርምጃ ብቻ “አዋጁ” በኢትዮጵያ 70 በመቶ የሚሆኑትን የሲቪል ማህበራት ድርጅቶችን ከስራ ውጭ አድርጓቸዋል፡፡ እ.ኤ.አ በፌብሯሪ 2010 ገዥው አካል ከተመሰረተ ብዙ ጊዚያትን ያስቆጠረውን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤን እና የኢትዮጵያ የህግ ባለሙያ ሴቶች ማህበርን በተጨባጭ የእነዚህን ሁለት ጠንካራ ተቋማት አቅም ሽባ ለማድረግ፣ እንዲሁም ደግሞ ሊያሳኩ የሚያስቧቸውን የተቋቋሙባቸውን ዝንባሌዎች እና ዓላማዎች ከህግ አግባብ ውጭ በሆነ መልኩ ለማስተጓጎል በማሰብ ሀብታቸውን እንዳያንቀሳቅሱ አገደ፡፡

የEITI የቦርድ አባላት እ.ኤ.ኤ በ2010 የገዥውን አካል የአባልነት ጥያቄ ውድቅ ካደረገ በኋላ በእርግጠኝነት አንድ ነገር ተለውጧል፡፡ እ.ኤ.አ በማርች 2011 ማዳም ክላሬ ሾርት የEITI የቦርድ ሊቀ መንበር ሆነው ተመርጠዋል፡፡ ማዳም ሾርት ለብዙ ጊዜ ተደናቂ መሪ እና በኢትዮጵያ ላለው ገዥ አካል ሻምፒዮን እንዲሁም በቅርቡ የአረፉት የአቶ መለስ ዜናዊ  ከፍተኛ አድናቂ ናቸው፡፡ በአቶ መለስ ዜናዊ ላይ ያመልካሉ፡፡ የሚያመልኳቸው ግን በጥሩ ነገር ተምሳሌትነታቸው አይደለም፡፡ ምናልባትም እ.ኤ.አ በ2010 ገዥው አካል የድርጅቱ አባል እንዳይሆን ውድቅ ያደረጉትን የEITI የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ተወካዮች እና የስራ ባልደረቦቻቸውን ክብር እና ሀሳብ ለማንኳሰስ እንዲሁም በወሰንየለሽ አፍቅሮ የተዘፈቁበትን ገዥ አካል ሽንፈት ለመበቀል ያደረጉት ሊሆን ይችላል ተብሎ ይገመታል፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የገዥው አካል የአባልነት ጥያቄ ውድቅ በተደረገበት ጊዜ በ EITI ታሪክ በእንደዚህ ያለ የአፋኝነት ህግ መሰረት “በግልጽ ከሰብአዊ መብት አጠባበቅ” ጋር በተያያዘ መልኩ አንዲት አገር የድርጅቱ አባል እንዳትሆን ውድቅ ሲደረግ የመጀመሪያው እና ብቸኛው ክስተት  ስለነበረም ነው፡፡ ማዳም ሾርት በአቶ መለስ ዜናዊ እና ኩባንያቸው ላይ የደረሰውን “ውርደት” ለመበቀል ዕቅድ በማውጣት በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ፊት የአቶ መለስን የመጀመሪያ የአባልነት ጥያቄ ውድቅ በማደረግ ቁልፍ ሚና የተጫወቱትን የEITI የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ተወካዮችን ማዋረድ ላይ ያጠነጠነ ነበር፡፡ ማዳም ክላሬ፣ በቀልተኛዋ አሁን የበቀል እርምጃዎን ወስደዋል፡፡!

ማዳም ክላሬ በኢትዮጵያ ላለው ገዥ አካል በመወገን እ.ኤ.አ ማርች 11/2014 ግልጽ ደብዳቤ በመጻፍ ድፍረት የተሞላበትን የዘመቻ ውትወታ (በማስገደድ አላልኩም) ሲጀምሩ በEITI በቦርድ አባልነት ባሉት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ተወካዮች እንደ አላዋቂ ልጅ አጥፊዎች ያህል አውርደው በመመልከት የቁጣ ድምጻቸውን ከፍ በማድረግ አምባርቀውባቸዋል፡፡ እብደትን የተላበሰ የሚያስገርም ምልከታም አድርገዋል፡፡ እንዲህ የሚል ምልከታ፣ “የEITI መርሆዎችን የሚተገብሩ አገሮችን ሁኔታ በመምለከትበት ጊዜ በኢትዮጵያ ያለው የሲቪል ማህበረሰብ ድርጀቶች ሁኔታ በሌሎች አገሮች ከሚታየው በብዙ መልኩ የከፋ ነው የሚለውን አባባል አልቀበለውም፣“ በማለት ለእራስ ታላቅ ክብርን የሰጠ የድንፋታ ንግግር አሰምተዋል፡፡ ማዳሟ ይህንን ንግግር ሲያደርጉ ምን ለማለት ፈልገው ነው? ለመሆኑ የEITI አባላት እነማን ናቸው?

EITI በአሁኑ ጊዜ 40 ወይም ከዚያ በላይ የሚሆኑ አባል አገሮች አሉት፡፡ ብዙዎቹ አባል አገሮችም በዓለም ላይ በሙስና በበከቱ እና ጨቋኝ መንግስታት መዳፍ ስር እግር ከወርች ተተብትበው የሚገኙ ናቸው፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አፍጋኒስታን፣ ቡርኪናፋሶ፣ ካሜሩን፣ የመካከለኛው አፍሪካ ሬፑብሊክ፣ ቻድ፣ የኮንጎ ዴሞክራቲክ ሬፑብሊክ፣ ጊኒ፣ ካዛኪስታን፣ ላይቤሪያ፣ ማሊ፣ ማውሪታንያ፣ ሞዛምቢክ፣ ኒጀር፣ ናይጀሪያ፣ የኮንጎ ሬፑበሊክ፣ ሴኔጋል፣ ሴራሊዮን፣ ታዣኪስታን እና የመን ይገኙበታል፡፡ “የኢትዮጵያ ሁኔታ ከሌሎች የከፋ አይደለም” ከሚለው ማነጻጸሪያቸው አንጻር ማዳም ሾርት በእርግጠኝነት አንድ ሊካድ የማይችል ሀቅን ተናግረዋል፣ ይኸውም በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል ከሌሎች በገፍ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣ ከሚፈጽሙት የEITI አባል አምባገነን አገሮች የከፋ አይደለም፣ ወይም ደግሞ ከብዙዎቹ የተለየ አይደለም ብለዋል፡፡ ሁሉም በሙስና የበከቱ ናቸው፡፡ ሁሉም የሲቪል ማህበረሰብ ተቋማትን ህልውና ግብአተ መሬት የፈጸሙ ናቸው፡፡ እናም የመመንተፊያ የቆዳ ቦርሳዎችን ተሸክመው ክው ክው የሚሉ ዘራፊዎች እና ወሮበሎች ናቸው፡፡ ማዳሟ ለቦርድ አባላቱ፣ ለሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እና ለኢትዮጵያውያን/ት የዲያስፖራ ማህበረሰብ አባላት ለማስተላለፍ የፈጉት ትክክለኛው መልዕክት ግልጽ ነበር፡፡ “ሁሉንም ጸጥ ለማድረግ” ነው፡፡ ከተሰጣችሁ ቁመት በላይ አትንጠራሩ፡፡ በሙስና የበከቱ ዘራፊዎችን ሊፒስቲክስ በመቀባት የተለመደውን የቢዝነስ ስራ እናስቀጥል፡፡ በዚህ መንገድ መጓዝ አንችልምን?

ባራክ ኦባማ እጩ ፕሬዚዳንታዊ ተመራጭ በነበሩበት ጊዜ ከተናገሩት ጋር እስማማለሁ፣ “አሳማን ለማቆንጀት ሊፒስቲክ (የከንፈር ቀለም) መቀባት ይቻላል፣ ሆኖም ግን አሁንም ያው አሳማ ነው፡፡ አንድን ትልቅ አሳ በወረቀት መጠቅለል ይቻላል፣ እናም ለውጥ ብለን ልንጠራው እንችላለን፣ ሆኖም ግን መጠንባቱን አያቆምም ፡፡“ EITI ለዘራፊዎች በልክ ዩኒፎርም አሰፍቶ ማስመሰያ በማልበስ “ግልጽነት” እና “ተጠያቂነት” ብሎ ሊጠራቸው ይችላል፣ ሆኖም ግን ያው አሁንም ዘራፊዎች ናቸው፡፡ ሙስናን በEITI አርማ መጠቅለል ይቻላል እናም ንጹህ ብሎ መጥራት ይቻላል፣ ሆኖም ግን እስከ አሁንም መጠንባቱን አያቆምም ፡፡ EITI የአፍሪካ ዘራፊ ገዥዎችን ንጹህ እና ጨዋ ለማስመሰል የሚቀባ ሊፒስቲክ ነው፡፡

አዲስ በሆነ መልኩ ማዳም ሾርት በእርግጠኝነት ትክክል ናቸው፡፡ ለተፈጠረው ስህተት ይቅርታ እጠይቃለሁ! ብዙዎቹ በEITI አባል የሆኑ የአፍሪካ አገሮች በተኩላ ዘራፊ ሙሰኛ ገዥ ቡድኖች የሚሽከረከሩ ናቸው፡፡ “ዘራፊነት የአፍሪካ አምባገነናዊነት ከፍተኛው ደረጃ” በሚል ርዕስ ባቀረብኩት ትችት ህልዮት ቀምሬ ነበር፡፡ ማዳም ሾርት በገንዘቡ በኩል ትክክል ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ያለውን ዘራፊ ገዥ አካል በEITI ካለው ከትክክለኛ ቦታው ታላቁ የሙስና ጠረጴዛ ላይ ለምን ነጠሉት? በእውነት ይህ ጉዳይ ፍትሀዊ አይደለም፡፡

የበለጠ ከዚህ በተለየ መልኩ ማዳም ሾርት የእኔን ነጥብ በትክክል አረጋግጠውታል፡፡ በእርግጥ EITI ማዕከላዊ የማዕድን ሙስና ቡድን ነው፡፡ አሊባባን እና 40ዎቹን ሌቦች አስታወሰኝ፡፡

አሁንም በጣም በተለየ መልኩ ማዳም ሾርት በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል የአባልነት ጥያቄው ተቀባይነት እንዲያገኝ እና በEITI ሲስተም እንዲገባ ለማድረግ በግልጽ ደብዳቢያቸው ላከናወኑት የሞት የሽረት ትግል በጣም ላመሰግናቸው እፈልጋለሁ፡፡ ከልብ በመነጨ መልክ ላደረጉት የትግል መንፈስ አደንቃቸዋለሁ፡፡ ማዳም ሾርት በእርሳቸው መንገድ የማይቆሙትን ማንንም ቢሆን የማዋረድ ስብእና ያላቸው ሰው ናቸው፡፡

የገዥውን አካል የአባልነት ጥያቄ ቦርዱ እንዲያጸድቀው በማስገደድ ማዳም ሾርት ታላቅ አገልግሎት አበርክተውልናል፡፡ ምንም በውል ሳያጤኑት EITI በእውን ምን ዓይነት ተቋም እንደሆነ እንዲሁም በህገወጥ መንገድ ጥቅም ለማግኘት የማስጠበቂያ የጫጫታ ቡድን መሆኑን አጋልጠዋል፡፡ በተደራጁ የወንጀለኞች ድርጅቶች የጥቅም ማስጠበቂያ የጫጫታ ቡድኖች የፖሊስ እና የፍትህ አካላቱ በትክክል ህዝቡን ማገልገል ሲሳናቸው ወይም ደግሞ ለማህበረሰቡ የህግ ጥበቃ ማቅረብ ሳይችሉ ሲቀሩ የሚከሰቱ ናቸው፡፡ “በጥቂት የክፍያ ገንዘብ” ሰበብ በሸፍጥ የተካነው ወንጀለኛ ለደንበኞቹ “ህግ እና ስርዓትን” ያስከብራል፣ እናም በሌሎች ወሮበሎች እና አዲስ ወንጀለኞች እንዳይዘረፉ ጥበቃውን ሊያረጋግጥ ይችላል፡፡

አብዛኞቹ የEITI አባል አገሮች በራሳቸው የህግ ተቋማት ሙስናን የመቆጣጠር አቅሙ የላቸውም፡፡ ብዙዎቹ አባል አገሮችም የአንድ ሰው፣ የአንድ ፓርቲ የፈላጭ ቆራጭነት ስርዓትን የሚያራምዱ ናቸው፡፡ የፖለቲካ ተቋማቱ እስከ አጥንታቸው ድረስ በዘለቀ የሙስና ነቀርሳ የበከቱ ናቸው፡፡ የይስሙላ ፓርላሜንታሪ ስርዓቶች አሏቸው፡፡ አቃቢያነ ህጎቻቸው በትምህርት፣ በማህበራዊ እና በሞራል ስብዕና አቅመቢስ የሆኑ ድሁር ወሮበላ ዘራፊዎች እና ጽናት የሌላቸው የእመኑልኝ የህግ መጽሐፍትን በብብታቸው ሸጉጠው የሚዞሩ የፓርቲ አባላት ናቸው፡፡ የፍትህ ስርዓቱ ከገዥው አካል አመራሮች የኋላ ኪስ የሚገኝ ስርዓት ነው፡፡ የጸረ ሙስና ኮሚሽኖች የፖሊቲካ ተቀናቃኞቻቸውን፣ በገዥው አካል ላይ የሚነሳሱትን ሰላማዊ አመጸኞችን ጨምሮ ለማጥቂያነት በእራስ የተሞሉ የርቀት አነጣጣሪ ሚሳይሎች ናቸው፡፡ የህግ የበላይነት የለም፣ ያለው የደናቁርት የዘራፊዎች ህግ ብቻ ነው፡፡

በአሁኑ ጊዜ EITI  በአፍሪካ እና በሌሎችም አገሮች ለዘመናት የሚዘልቅ የማዕድን ሙስና የተንሰራፋበት አዲስ ዓለም አቀፋዊ ስርዓት ለማንበር ዝግጅቱን አጠናቅቋል፡፡ ላለፉት አስርት ዓመታት EITI ያከናወናቸው ተግባራት እንግዲህ ይህንን ጉዳይ እውን ለማድረግ ነው፡፡ እውነት ለመናገር EITI  በእራሱ የሙስና ቡድን በሙስና የተዘፈቁ ገዥዎችን ለመከላከል የተቋቋመ ቡድን ነው፡፡ የአገራቸውን የተፈጥሮ ሀብት የዘረፉትን እና የመዘበሩትን ወሮበላ ዘራፊዎች መልሶ ለመዝረፍ የተቋቋመ ሰላማዊ ድርጅት ነው፡፡ ሁሉም በሙስና የተዘፈቁ ገዥ አካላት እንደገና ለመወለድ እና የEITIን ስርዎ መንግስት ለመቀዳጀት የሚከተሉትን ሂደቶች መከተል ይጠበቅባቸዋል፡፡ 1ኛ) የአባልነት መጠየቂያ ቅጹን መፈረም እና የEITIን የጥያቄ እና መልስ መዝሙሩን ደጋግሞ ማነብነብ፣ 2ኛ) መጠመቅ እና በ EITI ቄሶቹ መቀባት፣ 3ኛ) ቀደም ሲል ለተሰሩት ጥፋቶች በህዝብ ፊት ጥቂት ንስሀ የመግባት ተግባራትን ማከናወን፣ 4ኛ) ቀደም ሲል ለተፈጸሙ የሙስና ተግባራት ሁሉ ይቅርታ ማድረግ፣ 5ኛ) ከሙስና ወደ ንጹህነት እስኪመለሱ ድረስ የሶስት ዓመታት የዝግጅት ጊዜ መስጠት የሚሉት ናቸው፡፡

ለዘራፊ ገዥ አካላት ይህ ታላቅ ቅሌት ነው፡፡ የEITIን የከሀዲነት ባጅ ለማጥለቅ እና ከሙስና ምን ያህለ ነጻ እንደሆኑ በባዶ ኩራት በታጀለ መልኩ ለማሳመን በዝግጅት ላይ ናቸው፡፡  የEITI ባጅ በኢትዮጵያ ላሉት በሙስና የተዘፈቁ ዘራፊዎች የባዶ ዲስኩር የጉራ ችርቸራ  መብትን ያጎናጽፋቸዋል፡፡ የEITIን የአባልነት ፈቃድ በማግኘት በዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እና በኢትዮጵያውያን/ት የዲያስፖራ ማህበረሰብ አባላት ላይ በእውነተኛነት ላይ ተመስርቶ የተገኘ ፈቃድ አስመስሎ ለመቅረብ በሸፍጥነት መጠቀሚያ ያድርጉታል፡፡ ” ሂዩማን ራይትስ ዎች አፍንጫችሁን ላሱ! የኢትዮጵያ የዲያስፖራ አፍንጫችሁን ላሱ! እዩ እንግዲህ ተመልከቱ እንደ አዳኝ ውሻ ጥርስ ንጹህ ነን እናም ከዚህ በላይ ማረጋገጫ የለም ይህንን ልናረጋግጥላችሁ እንችላለን!“:: የማዕድን ሙስናውን ከጥርጣሬም በላይ ከተጨባጩ ሁኔታ በላይ፣ ከቦርዱ በላይ እና ከህግ በላይ አጠናክረው ይቀጥሉበታል፡፡ የEITI የአባልነት ፈቃድ በመስጠት ለመስረቅ፣ የተፈጥሮ ሀብትን ታማኝነት በጎደለው የጮሌነት አካሄድ ጥቅምን ለማግበስበስ ለማይጠረጠሩ ባለሀብቶች በመስጠት የሞራል ልዕልና በጎደለው መልኩ ተበዳሪዎችን እና ለጋሽ ድርጅቶችን በመጭመቅ ሌላ ተጨማሪ ገንዘብ ማጋበስን የሚያስችል መብትን ይሰጣቸዋል፡፡

የEITI አባል ለመሆን የተዘጋጁት ደረጃዎቹ እና መስፈርቶቹ ጸጥ የማድረጊያ የማስመሰያነት ዘዴዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ጸጥ የማድረጊያ ስልቶች ከውጭ የሚሰነዘሩባቸውን ትችቶች ለመሸበብ ብቻ አይደለም የተዘጋጁት ሆኖም ግን ከውስጥ ለሚነሱባቸው ሰላማዊ አመጾች ማዳፈኛ  እንዲሆኑ ጭምር እንጅ፡፡ EITI በአሰልች እና ተደጋጋሚነት ባለው የቢሮክራሲ ውጣውረድ የተተበተበ ፍሬከርስኪ የበዛበት የአባልነት መቀበያ መስፈርቶች፣ ተጠያቂነት እና ግልጸኝነት ያለው መሆኑን ከጉራ ባልዘለለ መልኩ ዲስኩር ሲያደርግ ይደመጣል፡፡ ማዳም ሾርት ግልጽ ደብዳቤ ብለው አዘጋጅተው በለቀቁት ደብዳቤ ላይ ለድርጅቱ እጩነት ለመብቃት “ከEITI ጋር አብሮ ለመስራት በግልጽ እና በቀላል መንገድ ለሲቪል ማህበረሰብ ድርቶች በቂ ምህዳር መኖር አለመኖሩ” ሁሉንም የህዝብ ግንኙት ስራዎች ሁሉ አፈር ድሜ አብልተውታል፡፡ ሌሎችስ በጣም አስመሳይ የሆኑ የባለስልጣን መስፈርቶች እንዴት ይታያሉ? እንዲሁ ዝም ብሎ የባህላዊ ጭፈራ እና ዳንስ ነውን?

በማንኛውም ትክክለኛ በሆነ መለኪያ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል የEITI አባልነት ተቀባይነት ማግኘት የድርጅቱ መስፈርቶች ባዶ እና ወና መሆናቸውን ያመላክታል፡፡ EITI የእራሱን ቡድን ለመቀላቀል “አንድ መንግስት የድርጅቱ አባል ሲሆን ምን መስራት እንዳለበት እምነቱን የሚገልጽ እና EITIን ለማጠናከር ያለውን ጽኑ የሆነ መግለጫ አዘጋጅቶ ማቅረብ ይጠበቅበታል፡፡” እውነት! ትልቅ ነገር! በመቀጠልም መንግስት “የEITIን ተግባራት ለማከናወን ሃላፊነት ያለው ከፍተኛ ባለስልጣን መሾም አለበት፡፡” እርግጥ ነው ሙሰኛ አሻንጉሊት የድርጅቱን ተግባራት መከናወናቸውን የሚከታተል ሌላ ሙሰኛ አሻንጉሊት ይሾማል፡፡ መንግስት “ከሲቪል ማህበረሰቡ ጋር መስራት ይጠበቅበታል፡፡” የትኛው ሲቪል ማህበረሰብ? ምንም ችግር የለም፡፡ ሙሰኛ ዘራፊዎች በሀገሮቻቸው ውስጥ እውነተኛ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ስለሚያጠፏቸው እነዚህ ዘራፊዎች ለእነርሱ የሚበጁትን የይስሙላ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች መቀፍቀፍ እንዲችሉ የፈቃድ ሰርቲፊኬቱን EITI ይሰጣቸዋል፡፡ ለዚህም ነው በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል የ “ኢትዮጵያ ብሄራዊ የጋዜጠኞች ህብረት” የሚል ሆድአደር ተለጣፊ ድርጅት በመፍጠር ሌሎችን እያሳደደ በማጥፋት ላይ ያለው፡፡ እንዲህ ያለ ቀልድ!

ከመሀል አዲስ አበባ ወጣ ብሎ የሚገኘው የአቶ መለስ የቃሊቲው የእስረኞች የማጎሪያ ማዕከል እውነተኛ ለፍትህ እና ለሀቅ የቆሙ ዕውቅናን ያተረፉ ጋዜጠኞች እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ ውድ እና ላቅ ያለ ደረጃ ያላቸውን ዓለም አቀፍ ሽልማቶች እየተቀበሉ የሚገኙት በርካታ ጋዜጠኞች እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት ዓለሙ እና ውብሸት ታዬ የመሳሰሉትን ጀግና ጋዜጠኞች ውጦ የምጻት ቀኑን የሚጠባበቅ የሰላማዊ ዜጎች የማሰቃያ ተቋም ነው፡፡ እስክንድር ነጋ በቅርቡ በህይወት በተለዩት በአቶ መለስ ዜናዊ ላይ ትችት በማቅረቡ እና በአረቡ ዓለም እየተካሄደ ባለው የጸደይ አብዮትን በማስመልከት በሰጠው ትንታኔ ብቻ ለ18 ዓመታት በእስር ቤት እንዲማቅቅ ያለምንም ሀፍረት ተበይኖበታል፡፡ ርዕዮት ዓለሙ እና ውብሸት ታዬ በየሳምንቱ በሚወጣ መጽሄት ላይ ሀሳባቸውን በመግለጻቸው ብቻ እያንዳንዳቸው በ14 ዓመታት እስር እንዲቀጡ በማንአለብኝነት በይስሙላው/የዝንጀሮ ፍርድ ቤት ህሊናየለሽ ውሳኔ ተበይኖባቸዋል፡፡

ከተለጣፊው “ከኢትዮጵያ ብሄራዊ የጋዜጠኞች ህብረት” ስለኢትዮጵያ የማዕድን ዘርፍ የተጠያቂነት እና ግልጸኝነት ትክክለኛ መረጃ ለማግኘት መጠበቅ ማለት የዶሮዎችን መጠለያ ቤት እንዲጠብቅ ኃላፊነት ከሚሰጠው ቀበሮ አንድም ዶሮ ላለመጥፋቱ ትክክለኛ የሂሳብ ሪፖርት እንዲያቀርብ መጠየቅ እንደማለት ነው፡፡ በEITI ገዥ አካሎች መሰረታዊ ሀሳብ መሰረት ህብረተሰቡን ያለምንም ተጽዕኖ የበላይ ተመልካችነት እና የተቆጣጣሪነት ስልጣን በመስጠት በቀጥታ ተሳታፊ በማድረግ በማዕድን እና በተፈጥሮ ጋዝ ዘርፉ ላይ ትክክለኛ እና በዘርፉ ሊረጋገጥ የሚችል መረጃን አዘጋጅቶ የማውጣት ስራን በማቀላጠፍ ሂደቱን የማሳለጥ ተግባራትን የማከናወን ስራ ነው፡፡ የዚህ ሁሉ የመጨረሻው ግቡ ደግሞ “ከተፈጥሮ ሀብት ተፈብርኮ የሚገኘው የምርት ገቢ በትክክል ያለምንም ሙስና ለህዝቡ ጥቅም እንዲውል መራጋገጫ የሚሰጥ ነው፡፡”

መረጃን በተመለከተ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል አስቀያሚ የመረጃ መቀቀያ ቶፋ አለው፡፡ “የአቶ መለስ ዜናዊ ምዕናባዊ የምጣኔ ሀብት“ እና “የአቶ መለስ ዜናዊ የውሸት የምጣኔ ሀብት” በሚሉ ርዕሶች ሳቀርብ እንደነበረ ሁሉ የአቶ መለስ ዜናዊ አገዛዝ በእርሳቸው አመራር ኢትዮጵያ አስር ዓመት  ሙሉ ያለምንም ማቋረጥ “ባለሁለት አሀዝ የኢኮኖሚ መጣኔ ዕድገት አስመዘገበች” በማለት ለፖለቲካ ፍጆታ ሲባል ብቻ የውሸት መረጃ በመረጃ መቀቀያው ቶፋ እየታጨቀ የሀሰት መረጃ ሲሰራጭ ቆይቷል፡፡ እውነታው ግን ላም አለኝ በሰማይ ነው፡፡ ብዙሀኑ የኢትዮጵያ ህዝብ አይደለም በቀን ሶስት ጊዜ አንድ ጊዜ እንኳን ለመብላት እየተቸገረ ነው ያለው፡፡

በጣም የሚያስደንቀው ነገር ደግሞ አቶ መለስ በብልጣብልጥነት የእራሳቸውን የቅጥፍና የኢኮኖሚ የዕድገት መረጃ አሀዝ ለዓለም ባንክ እና ለዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት የመመገባቸው ጉዳይ ይህንንም ተከትሎ እነዚህ ዓለም አቀፍ ተቋማት የእርሳቸውን ጥሩንባ የመንፋታቸው ጉዳይ ነው፡፡ እነዚህ ዓለም አቀፍ ተቋማት ከማንም በተሻለ መልክ ግንዛቤው ያላቸው ቢሆንም የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ ታላቅ እና ድፍረት የተሞላበት የውሸት የኢኮኖሚ ዘገባ በማቅረብ ወንጀለኛ ገዥ አካላት ዕኩይ ድርጊታቸው የሀሰት ዘገባዎችን እንዲያቀርቡ እየገዟቸው ይገኛሉ፡፡

በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል  በEITI የቀሚስ ጉንፍ ውስጥ ተወሽቆ በማዕድኑ ምርት እና ገቢ ሁሉምን ዓይነት የሀሰት የመረጃ አሀዞችን በመቀፍቀፍ እንዲሁም በሚሊዮኖች የሚቆጠር አንጡራ የሀገሪቱን ሀብት ወደ ውጭ በማሸሽ ውጭ አገር በሚገኙ የግል የባንክ ሂሳቦቻቸው ላይ በማስቀመጥ ላይ እንደሆኑ እና እንደዚህ ያሉ ተመሳሳይ የማታለል ድርጊቶችን በመፈጸም ላይ እንደሚገኙ የክርክር ጭብጤን ላቀርብ እችላለሁ፡፡ ወደፊት “በEITI ጋሻጃግሬነት እየተካሄደ ያለ የኢትዮጵያ የማዕድን ሙስና ተምኔታዊ የመረጃ አሃዞች” በሚል ርዕስ ስር ትችት አቀርባለሁ የሚል ዕቅድ አለኝ፡፡

EITI  ጥሩ የሚመስሉ መስፈርቶችን በማቅረብ ሆኖም ግን በአፍሪካ እና በሌሎች ታዳጊ አገሮች ለሚካሄዱት የአምራች ኢንዱስትሪዎች ሙስና የህጋዊነት ሽፋን በመስጠት የህጋዊነት ሀሳባዊነትን፣ ታማኝነትን ግልጽነት እና ተጠያቂነት ለመፍጠር ዓላማ ያደረገ ነው፡፡ EITI “የድብቅ ቴክኖሎጅን” የሚጠቀም በመሆኑ በአፍሪካ እና በሌላው ዓለም ያሉ በሙስና የተዘፈቁ ገዥ አካላት ያለምንም ስጋት እና ጥርጣሬ የህዝቦቻቸውን ሀብቶች ለመዝረፍ ሲሉ ተቋሙን መቀላቀል ይፈልጉታል፡፡ EITI እምነት ከማይጣልባቸው፣ በሙስና ከተዘፈቁ እና አስጸያፊ ባህሪያትን የተላበሱ፣ እንዲሁም ከብዙ ጊዜ ጀምሮ በዓለም መድረክ ላይ በመጀመሪያ እምነቱን በማግኘት በኋላ የሚከዳበት ዓይነት ጨዋታ ከሚደረግባቸው ድርጅቶች መካከል አንደኛው ነው ማለት ይቻላል፡፡

ሁለት ጊዜ ይቅርታ መጠየቅ እና አንዱን በጽናት መያዝ፣

“የማዕድን ሙስና በኢትዮጵያ፡ ለማዳም ክላሬ የተሰጠ መልስ” በሚለው የመጀመሪያው ትችቴ ላይ ማዳም ክላሬ የኢትዮጵያን የEITI አባል መሆን አስመልክቶ የዲያስፖራ ማህበረሰብ አባላት ከጉዳዩ ውጭ እንዲሆኑ ስላደረጓቸው አሰልች ቀኖናዊ ህጎች ለዲያስፖራው ማህበረሰብ ይቅርታ እንዲያቀርቡ ሀሳብ አቅርቤ ነበር፡፡ ማዳሟ “የቦርድ አባላቱ የኢትዮጵያን የተባበረ የሲቪል ማህበረሰብ ድምጽ እንጅ የተቃዋሚ ዲያስፖራ ድምጾችን መስማት እንደሌለበት ተማጽዕኖ አቅርበው ነበር፡፡” ውጤታማ በሆነ መልኩም የኢትዮጵያ ዲያስፖራ ድምጽ መዘጋት  እንዳለበት ሞግተዋል፡፡

“ግልጽ እና የተባበረው የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ” የማዳም ሾርት ፍጹም የሆነ ምዕናባዊ የሆነ እና የተረጋጋ ስሜት እንዳይኖር በማድረግ ዓላማ ላይ የሚሽከረከር ሆኖ ይገኛል፡፡ ትክክለኞቹ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ከዓመታት በፊት ጀምሮ ታፍነው ተሸብበው  ይገኛሉ፡፡ ሆኖም ግን ማዳም ሾርት በአንድ ወይም በሌላ ምክንያት በኢትዮጵያ የሲቪል ማህበረሰብ የሌለውን አለ የሚል ቅዠት ለማንበር ይፈልጋሉ፡፡ ምናልባትም የእርሳቸው የስሜት ጓደኛ እንደሆኑት እንደ አቶ መለስ ዜናዊ የመኝታ ጊዜ ትረካዎችን መናገር መውደድ አለባቸው፡፡ እኔ በትረካዎች ላይ በእርግጠኝነት ትዕግስት ማድረግን እከተላለሁ፣ እንደ ዶ/ር ሰውስ ተረት:- “ ተረት ተረት የላም በረት: አንድ ዓሳ፡፡ ሁለት ዓሳዎች፡፡ ቀይ ዓሳ፡፡ ሰማያዊ ዓሳ፡፡” ተረት ተረት አንድ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅት፡፡ ሁለት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች፡፡ ሰማያዊ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅት፡፡

በእርግጠኝነት ለተቀደሰ ተግባር፣ የተከበረ እና ሩህሩህነት የተንጸባረቀበት ሀሳብ ሲባል ማዳም ሾርት ለዲያስፖራ ኢትዮጵያውያን/ት የይቅርታ ደብዳቤ ማስገባት ይኖርባቸዋል የሚል ተስፋ ነበረኝ፡፡ ምናልባትም “ከተናገርኩት ውጭ የስህተት ግንዛቤ ተይዟል ይቅርታ” ሊሉ ይችሉ ይሆናል፡፡ እንደ ቆንጆ የህዝብ ግንኙነት ስራ በእርግጠኝነት ላይሉም ይችላሉ፡፡ ማዳም በእርሳቸው የተዛባ ጥላቻ  ሰበብ የጥቃት ሰለባ ለሆኑት ወገኖች ይቅርታ ለመጠየቅ ለጋስነቱ ያላቸው አይመስልም፡፡ የዘመኑን የወጣቶችን ንግግር ለመጠቀም ማዳም ሾርት ሰዎችን በመበጥበጥ ከዘራፊዎች ድንበር ተርታ ጋር የሚያመሳስል የረዥም ጊዜ እውቅና አላቸው፡፡ ማዳም ሾርት በብርሀን ፍጥነት ተናዳጅነታቸው እና ግንፍልተኝነታቸው ይታወቃሉ፡፡ ሪቻርድ ዶውደን የተባለው የእንግሊዝ ታዋቂ ጋዜጠኛ እ.ኤ.አ በ2011 ከማዳም ሾርት ትረካውን እንዲህ አቅርቦታል፡፡ “በአንድ ወቅት በአውሮፕላን ላይ ቃለ መጠይቅ እያደረግሁላቸው ሳለ እና ስለሩዋንዳ የሰብአዊ መብት ሁኔታ ትኩረት በመስጠት ጥያቄዬን ሳቀርብ ማዳሟ እኔን ለመወርወር በሚያስችል ዓይነት ሁኔታ አስፈራሩኝ፡፡ በዚያን ወቅት በጊኒ የአየር ክልል ላይ ስለነበርን ከዚያ በኋላ አቆምኩ፡፡ አሁን ደግሞ የተዋበ፣ ሰላም እና መረጋጋት በሰፈነበት በለንደን የጋራ ሀብት ክለብ ተገናኘን፣ እናም ማዳሟ እርጋታ የሚታይባቸው እና ሀሳብ የሚሰጡ ሆኖም ግን በማንም ዘንድ ጠንካራ ትችት የሚያቀርቡ የሚያደርጉትንም በብልኃት መያዝ የማይችሉ ሆነው ነው ያገኘኋቸው፡፡“ ማዳም ሾርት ቀልድ አያውቁም! ቶኒ ብሌር ሃሰባቸውን እንዳይገልጹ ለማድረግ በሀይል አፋቸውን ያስይዟቸው ነበር፡፡ (ብሌር የተናገሩት አያስደነቅም:- ”እንደተዋረደች እና ሀሳቧን እንዳትገልጽ በኃይል እንደተያዘች ሚስት ነው የተሰማኝ፡፡” ያሉት ሲያመናጭቁአቸው:: ይህ አካሄድ የማዳም ሾርት አጭሩ ጎዳና ነው! ቢሆንም ለማዳሟ ክብር እሰጣቸዋለሁ፡፡ ለሚያምኑት ይቆማሉ: ይዋጋሉ:: በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ላሉት ገዥ ዘራፊዎች በጽናት ይቅርታ የሚያቀርቡ ሴት ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ የዲያስፖራ ማህበረሰብ አባላትን ይቅርታ መጠየቅ አስፈላጊ አይደለም፡፡ ሆኖም ግን ማዳም ሾርት በድርጅታቸው ያሉትን የሰቪል ማህበረሰብ ድርጅት ተወካዮችን ማለትም ዓሊ ኢድሪሳን፣ ንዋዲሺን ጂን ክላውዲ ካቴንዴን እና ሌሎችን የከፈለህን አትም አባላት ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡ ይህንን በጥብቅ እጠይቃለሁ! ማዳሟ “በግልጽ ደብዳቢያቸው” ፍትህዊነትን በጣሰ መልኩ አስደናቂ ተዋንያን በመሆን በዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ላይ አምባርቀውባቸዋል፡፡ “የተለየ ፍላጎት ያላቸው ቡድኖች ጠንካራ ድምጾችን በማሰማት ተጽዕኖ ለመፍጠር የሚደረግ ጥረት እንዳለ እና እንዲያውም የሰሜን ደቡቡን እንዲወስንለት በታቀደ ዘይቤ የሚመሩ ናቸው በማለት ክስ አቅርበውባቸዋል፡፡” የኢትዮጵያ ገዥው አካል የEITI አባል እንዳይሆን ተቀዋሚዎች ተቃውሞ በማሰማት የEITIን ዕድል ተፈታትነዋል በማለት ማዳሟ ጩኸታቸውን አሰምተዋል፡፡

ኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴን በማክበር ለማዳም ሾርት ግልጽ ደብዳቤ ግልጽ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ እንዲህም ብለዋል፣ “የኢትዮጵያ የEITI የአባልነት ጥያቄ በቀጣናው ስብሰባ እዲቀርብ በአጀንዳችን ውስጥ አልነበረም በእርግጥ ይህ ጉዳይ የከባቢ ሁኔታ ግምገማዎችን እያደረግን ባለንበት ሁኔታ ነው የመጣው፡፡“ በወቅቱ ሁለት ገዥ ሀሳቦች ተነስተው አንደኛው በመቃወም ሁለተኛው ደግሞ በመደገፍ ክርክር እንደነበር ገልጸዋል፡፡ “ገለልተኛ” በሆነ መልኩ ማዳሟን እንዲህ በማለት ሞግተዋል፣ “ኢትዮጵያ የEITI አባል እንድትሆን ግልጽ አቋም በመያዝ  ወገንተኝነት አሳይተዋል፣ ከገለልተኝነት መርህ ጋር በተጻረረ መልኩ በድርጅቱ ሊቀመንበርነትዎ ላይ ጥያቄ ሊያስነሳ የሚችል ድርጊትን ፈጽመዋል፡፡ የድርጅቱ ታማኝ የመሆን ጠቀሜታ መሰረት የሚለካው በዚህ ጠቃሚ መርህ ነው፡፡” በዚህ አስፈሪ ግልጽ ደብዳቤ እንቆቅልሽ የሆነባቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡ “በዚህ ጉዳይ ላይ ግልጹ ደብዳቤ ለተውሰኑ ጥቂት ሰዎች ማሳወቅ ሲገባ ለምን ለህዝብ ይፋ እንደተደረገ ግልጽ አለመሆኑን ለመጠቆም እንፈልጋለን… እንደዚሁም የእኛም ደብዳቤ እርስዎ ለህዝብ ለአደባባይ እንዳቀረቡት ሁሉ በEITI ድረ ገጽ ላይ እንዲታተም እንጠይቃለን፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በሲቪል ማህበረሰብ ተወካዮች ዓለም አቀፍ ድረ ገጽ ለጥምረት አባሎቻችን በሙሉ ሊለቀቅ ይገባል፡፡“ የሚል ነው፡፡

ማዳም ሾርት ለኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴ በቀጥታ ሳይሆን በጸሐፊያቸው በጆናስ ሞበርግ በኩል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ የተሰጠው መልስ በቁስል ላይ ጨው  መነስነስ ያህል ነበር፡፡ ማዳሟ በግልጽ ደብዳቢያቸው ለኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴ ደብዳቤ መጻፉ ችግር እንደሌለባቸው በመጮህ የተናገሩ ሲሆን ቀደም ሲል የዓለም ማህበረሰብ ከማወቁ በፊት መደረግ እንደነበረበት ተናግረዋል፣ ሆኖም ግን በኋላ ደፍረው ሲመልሱ አንዴት ተደርጎ!? በተለመደው ቦታቸው አርፈው እንዲቀመጡ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሞበርግ ይህንን ቆሻሻ ስራ የተሰጠው ሰው ነው፡፡ እኔ በግሌ የሚከተለውን ሳነብ እንደተዋረድኩ እቆጥረዋለሁ፣

“ማዳም ክላሬ ለእናንተ ደብዳቤ ምላሽ እንድጽፍ ጠይቀውኛል፡፡ ያቀረባችኋቸው ነጥቦች በሙሉ ማስታወሻ ተይዞባቸዋል፣ የሊቀመንበሯን ገለልተኛነት ተብሎ ከሚጠራው ነጥብ በስተቀር፡፡ ለጂን ክላውዴ እንደገለጽኩት ሁሉ ሊቀመንበሯ ገለልተኛ እንዲሆኑ አይጠበቅባቸውም፡፡ እንደማንኛቸውም የእኛ ባለድርሻ አካላት ተወካዮች ሁሉ ገለልተኛ መሆን እንዳለባቸው አይነት በመሆን ሊሰሩ አይችሉም፡፡ ሊቀመንበሯ EITIን ነው የሚያገለግሉት ምክንያቱም በድርጅቱ መርሆዎች ላይ እምነት ስላላቸው ነው፡፡ እነዚህን መርሆዎች የመጠበቅ ኃላፊነት እና የEITIን ጥቅም ማስጠበቅ አለባቸው፣ እናም ለእናንተ ደብዳቤ በጻፉበት ወቅት ያደረጉት ነገር ቢኖር ይህንኑ ነው፡፡ በደብዳቢያቸው ላይ የሊቀመንበሯን ሚና የሚጥስ ነገር አልታየም፡፡”

ኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴ ከክብርትነታቸው በቀጥታ የሚጻፍ ደብዳቤ እንደክብርቷ አመለካከት ከሆነ አይመጥናቸውም፡፡ በሌላ አገላለጽ የማዳሟን ክብር ዝቅ የሚያደርግ ነገር ነው፡፡የሞበርግን ደብዳቤ በድጋሜ ሳነበው በጫካ እንደሚኖረው ባለረዥም ጅራት ቆርጣሚ አውሬ በንዴት ብግን ነው ያልኩት፡፡ ማዳም ሾርት ምን ያህል ደፋር መሆናቸውን የሚያሳየው በጸሐፊው አማካይነት ምላሽ የሰጡ መሆናቸውን ስናስተውል ነው! ማንም ጭራቃዊነት የሰራው እርሳቸው አይደሉምን?! በፍጹም የማለት ሞገስ ሊኖራቸው አይችልምን! ቀላሉ ዘዴ በጸሐፊያቸው አማካይነት የማርቀቅ እና እርሳቸው ፈርመው መላክ ነው፡፡ በግልጽ ለመናገር ማዳም ሾርት ለኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴ ግልጽ መልዕክት ማስተላለፍ ፈልገዋል፡፡ ማን አለቃ እንደሆነ እና አጠቃላይ ሁኔታውን ለማሳወቅ ፈልገዋል፡፡ እርሳቸው አለቃ ናቸው፣ ስለሆነም ስለማንኛውም ነገር ደንታ የላቸውም፡፡ እንደዚሁም ደግሞ ማዳም ሾርት ስለኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ስለካቴንዴ ጉዳይ ደንታ የላቸውም!

ስለሰው ልጅ ስብዕና፣ ክብር እና ሞገስ ስል በኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴ ስም እኔ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡ ከእነዚህ ሰዎች ጋር ተገናኝቸ ወይም ደግሞ ተነጋግሬ አላውቅም፡፡ ሆኖም ግን እንደ አንድ አፍሪካዊ ወገኖቼ የእነርሱ ውርደት የእኔም ውርደት እንደሆነ እንዲገነዘቡልኝ እፈልጋለሁ፡፡ በእንደዚያ ዓይነት አያያዝ ሲስተናገዱ ስመለከት እንደ አፍሪካዊ የእኔ ኩራት ጉዳት ደርሶበታል፡፡ ሆኖም ግን እንዲያውቁልኝ የምፈልገው ነገር ቢኖር ጠንካራ ኩራት እና ኃይል ይሰማኛል፡፡ ለማዳም ሾርት አስደንጋጭ ግልጽ ድብዳቤ የሰጡት ምላሽ የአስተዋይነት፣ የምክንያታዊነት እና የተለምዷዊ በጎ ምግባር ተምሳሌት ነበር፡፡ እነዚህ አፍሪካውያኑ በምላሻቸው ላይ ቁጥብነትን፣ ባለሞያነትን፣ታጋሽነትን እና ታማኝነትን አሳይተዋል፡፡ እንደዚሁም ደግሞ “አፍሪካዊ ትውልዶቻቸው እሺ! አቤት ወዴት! እርስዎ እንዳሉት ጌታዬ!” እያሉ ስብዕናቸውን ዝቅ ማድረግ በፍጹም እንደሌለባቸው በተጨባጭ አሳይተዋል፡፡ ማዳም ሾርት እና መሰሎቻቸው አዲሱ የአፍሪካ ትውልድ ለማንም ሎሌ እንደማይሆን ሊገነዘቡ ይገባል፡፡ በአሁኑ ጊዜ ሰውን ባለቃነቱ ብቻ “አዎ አዳኙ ጌታዬ” የሚባለው ተረት ተረት ጊዜው ያለፈበት እና ያፈጀበት ዘመን ላይ ነን፡፡ ሁላችንም አፍሪካውያን በጀግኖቹ ኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴ ልንኮራ ይገባል፣ ምክንያቱም ክብርን በደፈጠጠ እና ባዋረደ ጭራቃዊ መንፈስ ላይ የብዕር ጦራቸውን በመስበቅ ክብር እና ሞገስን እንድንቀዳጅ አስችለውናል፡፡ በከፍተኛ ደረጃ የፈጸሙት ተግባር ነው፡፡ ይሄ ነው ጀግኖች! እናደንቃችኋለን ኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴ፡፡

በተጨማሪም ማዳም ሾርት በተደጋጋሚ በተናገሩት አቁሳይ እና ከስልጣን ገደባቸው ውጭ በመሄድ ላሳዩት ትዕቢት በተቀላቀለበት ድንፋታ ስሜታቸው እንዳይጎዳ መጽናናትን እንዲያደርጉ እማጸናለሁ፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ማዳም ሾርት በቅርቡ በህይወት የተለዩት የአቶ መለስ ዜናዊ አምላኪ ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ በኤፕሪል 2013 ማዳም ሾርት በአንድ የመታሰቢያ በዓል ላይ በመገኘት አቶ መለስ “ታላቁ” ሰው በማለት አድናቆታቸውን ገልጸዋል፡፡  እንዲህም ብለዋል፣ “አቶ መለስ በህይወት ዘመኔ ካየኋቸው ሁሉ የመጠቀ እውቀት ያላቸው ፖለቲከኛ ናቸው” በማለት አሞካሽተዋቸዋል፡፡ (ቶኒ ብሌር፣ ጎርደን ብራውን፣ ሃሬት ሃርማን፣ ኢድ ሚሊባንድ፣ ዴቪድ ካሜሩን፣ ጆህን ሜጀር፣ ታቼርን ቅርጫት ደፉባቸው፡፡ ማዳም ሾርት ደስ ያላልዎትን የሚያስጨንቀዎን ነገር መግለጽ ይችላሉ!) እኔ በበኩሌ “አቶ መለስ ሁሉን ነገር አዋቂ” መሆናቸውን አላውቅም፣ ይልቁንም አነጣጥሮ ገዳይ እና አስገዳይ ተራ እርባናቢስ ለሰው ክብር የሌላቸው ዉዳቂ የነበሩ ለመሆናቸው ቅንጣት ያህል ጥርጣሬ የለኝም፡፡ እስቲ አካባቢያችሁን ተመልከቱ፣ ሁሉም ጭራቸውን ይቆላሉ፡፡

አቶ መለስ እንደ ማዳም ሾርት ሁሉ እርሳቸውን የተቃወሟቸውን ወይም በእርሳቸው ላይ ትችት ያቀረቡትን ሁሉ “ድራሻቸውን የሚያጠፉ” በእብሪት የተሞሉ ሰው ነበሩ፡፡ የእርሳቸውን ተቀናቃኞች በተደጋጋሚ “ደደቦች”፣ “ቆሻሾች”፣ “የጭቃ ጅራፎች”፣ “ስግብግቦች” እና “ለምንም የማይጠቅሙ እርባና ቢሶች” በማለት ይፈርጇቸው ነበር፡፡ እንደዚሁም በሰለጠነ ህብረተሰብ አጠራር መሰረት ደግሞ ለመጥራት ጸያፍ የሆኑ ስሞችን ይለጥፉ ነበር፡፡ አቶ መለስ በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያዋ ሴት ሊቀመንበር የነበሩትን ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳን ወደ እስር ቤት ወርውረው ለብቻ በአንድ ክፍል ውስጥ እንዲታሰሩ ካደረጉ በኋላ እንቅስቃሴ ባለማድረጓ ምክንያት የመወፈር ነገር ይታይባታል የሚል ምጸት አሰምተዋል፡፡ አቶ መለስ በፓርላሜንት ጉባኤ ላይ የሚገዳደሩ ጥያቄዎችን በማንሳት ወይም ሌላ ለየት ያለ አካሄድ እንዳለ ለማሳየት ሀሳብ የሚያቀርቡ ተወካዮችን በማዋረድ እና በመዘለፍ በሚፈጽሟቸው ጭራቃዊ ድርጊቶቻቸው ይደሰቱ እና እርካታን ያገኙ ነበር፡፡ የእርሳቸው ሰውን አሳንሶ የመመልከት፣ ምጸታዊ ንግግር፣ እና ለሚጠየቋቸው ጥያቄዎች የሚሰጧቸው ንቀት የተሞሉባቸው መልሶች በጣም አዋራጅ እና የተጠየቁ ጠቃሚ ነገሮችን ነቅሰው በማውጣ መልስ እንዳያገኙ የመዝለል ሁኔታዎች አንዳንድ ድፍረት ያላቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ተወካዮች በድፍረት ለሚያቀርቧቸው ጥያቄዎች የሚሰጧቸው ምላሾች እና የመድረክ ተውኔቶች ነበሩ፡፡ እ.ኤ.አ በሜይ 2010 የተደረገውን ሀገር አቀፍ ምርጫ 99.6 በመቶ የተገኘው የድምጽ ውጤት በመጭበረበሩ ምክንያት የተገኘ መሆኑን የአውሮፓ ህብረት የታዛቢዎች ቡድን አቶ መለስን ከእውነታው ጋር አፋጥጠው ሲይዟቸው አቶ መለስ የአውሮፓ ህብረት የታዛቢዎች ቡድንን ዘገባ “ወደ ቅርጫት መጣል ያለበት ቆሻሻ ነው” በማለት በጅምላ አውግዘዋቸዋል፡፡ ምን ማለት እችላለሁ?  እራስን በአምላክነት ሰይሞ ተከታይ እንዲኖር መፈለግ!

ማዳም ሾርት EITI መርሆዎች እሰከብረዋል ወይስ ደግሞ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል ተሟጋች/ወኪል ነበሩ? 

ማዳም ሾርት በሞበርግ አማካይነት ለኢድሪሳ፣ ንዋዲሺ እና ካቴንዴ በሰጡት ምላሽ ለኢትዮጵያ ወገንተኛ ያልነበሩ ብቻ ሳይሆን የEITIን መርሆዎች ለማስጠበቅ እና ለEITI ጥቅም ተግተው በመስራት ኃላፊነታቸውን እንደሚወጡ የሚገልጽ ነበር፡፡ እርግጠኛ ነዎትን?

ማዳም ሾርት “የEITIን መርሆዎች አስጠብቀው” ነበር ወይስ ደግሞ በኢትዮጵያ ላለው ገዥ አካል ወግነው ነው ይህን የሚከተለውን ግልጽ ደብዳቤ የጻፉት የሚለውን ማየት ለግንዛቤ የበለጠ ይረዳል፡፡

በኢትዮጵያ ያለው የሲቪል ማህበረሰብ ሁኔታ ከሌሎች በርካታ አገሮች የከፋ ነው የሚለውን አልቀበለውም፡፡

በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ያለው ውይይት ጠቀሜታ በሌለው መንገድ የተለየ ፍላጎት ባላቸው እና ሙሉ ትርጉም ባለው “የሰሜኖች ለደቡቦች መናገር አለባቸው በሚለው የአሰራር ዘየ” በተገመደ ጠንካራ ድምጽ ተጽዕኖ ስር የወደቀ በመሆኑ ላይ መናገር አለብኝ፡፡

የአትዮጵያን የአባልነት ጥያቄ ውድቅ ማድረግ ማለት የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ የትም እንዳይሄዱ ማድረግ ማለት ነው፡፡

ከኢትዮጵያ የዲያስፖራ ማህበረሰብ ተቃውሞዎችን ከመስማት ይልቅ በኢትዮጵያ ግልጽ እና የተባበሩ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ድምጽ መስማት ያለብን በመሆኑ ላይ ያለኝን እምነት መግለጽ እፈልጋለሁ፡፡

በጥሩ ሁኔታ መስራት የሚችሉ በጣም ጠንካራ የሆኑ ሌሎችን የአፍሪካ አገሮች ሊቀላቀሉ የሚችሉ የሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች እንዳሉ ከሀሳባዊነት በራቀ መልኩ ምንም ዓይነት ጥርጥር የለኝም

አንድ ዓይነት ወጥነት የሌላቸው መስፈርቶች መኖርም ሌላው ታላቅ ችግር ነው፡፡ ለምሳሌ በሀገሬ የቅዱስ ፓውሎስ ካቴድራል ውጫዊ ክፍልን በኃይል የተቆጣጠሩትን ተቃዋሚዎች ማባረረን አስመልክቶ የሚነገር ጉምጉምታ አለ፡፡ የጓንታናሞ መኖር እና ማሰቃየትን የመተግበር ሁኔታ አስመልክቶ ዩናይትድ ስቴትስ ጉዳይ ለአባልነት ጥያቄ ሲቀርብ አልተነሳም፡፡

EITI የዘመቻ አድራጊዎች መሳሪያ ተደርጎ የሚታይ ከሆነ ውጤታማ እና ድጋፍ የሚኖረው ሊሆን አይችልም፡፡   

ጎራዴው ለምን ማጥቂያነት ይውላል? 

ማደም ሾርት ገዠው አካል የEITI አባል መሆን እንዲችል ጉሮሮ ለጉሮሮ በመተናነቅ ከፍተኛ ተጋድሎ አድርገዋል፡፡ በግልጽ ድብዳቢያቸው በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል አባል እንዲሆን ሽንጣቸውን ገትረው የውትወታ ተግባራቸውን አከናውነዋል፡፡ ማንም ሽንጡን ገትሮ ላመነበት ጉዳይ ትጋድሎ የሚያደርግን ሰው በሀሳብ የማንግባባ ቢሆንም እንኳን አከብራለሁ፡፡ ማዳም ሾርትም ላመኑበት ጉዳይ በጽናት መቆማቸውን አደንቃለሁ፡፡ ሆኖም ግን እደነቃለሁ፣ በእርግጥም በጣም እደነቃለሁ! ማዳሟ ላደረጉት የጽናት ተጋድሎ ዋጋቸው ምን ሊሆን ይችል ይሆን? በኢትዮጵያ ላሉ ዘራፊዎች ማዳም ሾርት ያደረጉት ተጋድሎ ዋጋ ምን ያህል ይሆን? የማዳም ነብስ ዋጋው ምን ያህል ይሆን?

በእርግጠኘነት ስለEITI ከልብ የሚቆረቆረው ማን ነው?

EITI፣ CCC፣ EEITI  ማንም ይሁን! ማን ነው ያገባኛል የሚለው? ማን ነው ትኩረት አድርጎ የሚይዘው!? አሳማን ሊፒስቲክ መቀባት ይቻላል፣ ሆኖም ግን አሁንም ያው አሳማ ነው፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ሁሉንም የአፍሪካ ዘራፊ አምባገነኖች የEITI አባል ማድረግ ይቻላል፣ እናም ግልጸኝነት እና ተጠያቂነት ብሎ መጥራት ይቻላል፡፡ በቀኑ መጫረሻም ያው አንድ ዓይነት ዩኒፎርም የተሰፋላቸው የዝርፊያ ቦርሳዎችን ይዘው የሚዞሩ ዘራፊ አምባገነኖች ናቸው፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ መሰቃየት፣ ኃይልን መጠቀም እና ጭካኔ ከጊዜ ወደ ጊዜ በመቀጠል ላይ ይገኛል፣

ማዳም ሾርት ለአንድ አፍታ እንዲህ በማለት አሰቡ፣ ”እኔ እንደማስበው መሰቃየቱ፣ በኃይል መጠቀም እና ጭካኔ የተሞላበት ሁኔታዎች በጓንታናሞ እስር ቤት እና በኢራቅ ላይ ቀጥለዋል፡፡“ ደህና፣ እንዲሁም ለኢትዮጵያ በተመሳሳይ መልኩ አስባለሁ፡፡ በኢትዮጵያ የሚደረገው ማሰቃየት፣ የኃይል እርምጃ እና ጭካኔ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀጠለ ነው፡፡ ጋዜጠኞች ይታሰራሉ፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ይዘጋሉ፣ የተቃዋሚ ፖለቲካ ድርጅት መሪዎች እንዲሸማቀቁ እና በፍርሀት ቆፈን እንዲጠመዱ እና እንዲታሰሩ ይደረጋሉ፣ ሰላማዊ አመጸኞች በኃይል እንዲጨፈለቁ ይደረጋሉ፣ እንዲሁም ምርጫዎች በጠራራ ጸሐይ ይጭበረበራሉ፡፡ ይህ ሁሉ ግን ሰላማዊ የሽግግር ለውጡን ሊያቆመው አይችልም፡፡ ያ ሁኔታ ይቀጥላል፣ ይቀጥላል… የኢትዮጵያ ወጣት ሴቶች እና ወንዶች ይነሳሉ እናም ለነጻነታቸው እንዲህ በማለት ይጮሃሉ፣

“ከዚህ በኋላ ትዕግስታችን ተሟጧል! ተርበናል! ነጻነት እንፈልጋለን! ነጻነት እንፈልጋለን! እስክንድር ይፈታ! አንዷለም ይፈታ! አቡባከር ይፈታ! ርዕዮት ትፈታ! የፖለቲካ እስረኞች በሙሉ ይፈቱ! ፍትህ እንፈልጋለን! ነጻነት! ነጻነት! ነጻነት! አትከፋፍሉን! ኢትዮጵያ አንድ ነች! አንድ ኢትዮጵያ! ከዚህ በኋላ ትዕግስታችን ተሟጧል! ውኃ ናፈቀን! መብራት ናፈቀን! ተርበናል!…“

በጓንታናሞ እና በኢራቅ ውስጥ የሚካሄዱትን ስቃዮች፣ የኃይል እርምጃዎች እና ጭካኔዎች በሚመለከት ማዳም ሾርት የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶችን ተጠያቂዎች እንዳደረጓቸው ሁሉ እኔ ደግሞ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ጠቅላላ ከጠፉ በኋላ ማዳም ሾርትን ተጠያቂ አደርጋለሁ፡፡

ማዳም ክላሬ ሾርት፣ተከሰዋል…!”

“እውነትን በዘጉ ጊዜ እና ከመሬትውስጥበቀበሯትቁጥር ድርጊቱን ማድረግ ይቻላል፣ ሆኖም ግን እውነት እያደገች፣ እየጠነከረች ትሄዳለች፣ እናም በአንድ ላይ ተሰባስባ የሚፈነዳ ኃይል ትፍጥራለች፣ በምትፈነዳበት ዕለት ሁሉም ነገር እራሷ በቀየሰችው መንገድ ይፈነዳል፡፡“ ኢሚሌ ዞላ

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

መጋቢት 16 ቀን 2006 ዓ.ም