ሰብአዊ መብት ለሰብአዊያን

ከፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም
ትርጉም ከነጻነት ለሃገሬ

በዓለም ዙርያ ያሉትን አንባቢዎቼን 2013 የደስታና የብልጽጋና ዓመት ይሁንላችሁ በማለት መልካም ምኞቴን እገልጻለሁ፡፡

ላለፉት ያልተቋረጡ 300 ሳምንታት ያህል ጦማሮቼን ለተከታተሉ ሁሉ፤ከልብ የመነጨ አክብሮቴንና ምስጋናዬን እገልጻለሁ፡፡ ከኢትዮጵያና ከዲያስፖራ ኢትዮጵያዊያን ለተቸረኝ ማበረታታት ምስጋናዬ ይድረስልኝ፡፡

አንባቢዎቼን፤ በኢትዮጵያና በዓለም ላይ ሁሉ የተደፈሩ ሰብአዊ መብቶችን ለሁሉም ሰብአዊ ፍጡራን እንዲዳረሱና እንዲከበሩ የመጠራሪያና የማንቂያ ደወል በአፍሪካና በዓለማቱ ሁሉ እንደውል እላለሁ፡፡ ዶክተር ማርቲን ሉተር ኪንግ አንዳሉት “በማይበጠስ የአንድነት ሰባዊ ሰንሰለት ተሳስረናል፡፡ በአንድ አይነት እጣ ፈንታ ተያይዘናል:: አንዱን በቀጥታ የሚያጠቃው ሌላውንም በተዘዋዋሪ ደግሞ አይተወውም፡፡

አንባቢዎቼን፤ በሎርድ አልፍሬድ ቴኒሰን የረቀቀ ለዛ ባለው ግጥም (“እንጠራራ፤ ለሰብአዊ ፍጡር ሁሉ”) አሮጌውን ዓመት በመሰናበት አዲሱን እንቀበል በማለት አጠይቃለሁ::

እንጠራራ፤ አሮጌውን አመት ለመሸኘት አዲሱን ለመቀበል

እንጠራራ፤ ሃሰትን ተገላግለን አውነትን ለማስገባት

እንጠራራ፤ ሃዘንና ትካዜን ከሕሊናችንን ለማስወገድ

እንጠራራ፤ በደሃና በሃብታም መሃል ያለዉን ቅራኔ ለመፍታት::

እንጠራራ፤ ለሰብአዊፍጡርሁሉአዲስስብእናእንተካለት::

እንጠራራ፤ የወደቀ ስራትን ለመሸኘት

ለመለወጥ ዘመን የሻረውን የፓርቲዎችን መናቆር

እንጠራራ የሕይወትን  ክቡርነት እናስመስክር

በጣፋጭ ባህል በንጹህ ሕግጋት::

እንጠራራ፤  አጉል ትምክህትን ለማጥፋት

በዜግነት ላይ ሀሜት ክፋትና እልህ እንዲወገድ

እንጠራራ፤  ፍቅርን ሃቅና እውነትን ለማስገባት

እንጠራራ፤ መልክምን ለመተግበር ለሁሉም በሚሆን መንገድ::

እንጠራራ፤ ያለፉትን ሺህ እልቂቶች ላለመድገም

እንጠራራ፤ ለቀጣዮቹ ሺህ ዓመታት ሰላም አንዲሰፍን

እንጠራራ፤ለነጻነት ወደሚያበቃን ጀግንነት

ለሩህሩህ ልብ፤ ለለጋሽ እጆች

እንጠራራ ጨለማ የዋጣትን ምድር ለማዳን::

2012ን ስንሸኘው: ባለፈው አመት ካቀረብክዋቸው ሳሚንታዊ  ጽሁፎቼ  ትንሽ  ቅንጣቢ በመውሰድ ነው::

በጃንዋሪ 2012 የአፍሪካ ስፕሪንግ አለያም ‹‹የኢትዮጵያ ጸደይ›› ይመጣ እንደሆነ በማለት አግራሞቴን ጎላ አድርጌ አሰምቼ ነበር፡፡

የራሴን ጥያቄ በአልበርት ካሙስ ‹‹ዘ ሪቤል›› (ተቃዋሚ) በተባለው መጽሃፍ ሚስጥራዊ ትርጉም ውስጥ ሆኜ  መልሼ ነበር፡፡ ተቃዋሚ ምንድን ነው? ሲል ጠየቀ ካሙስ………… ‹‹እምቢ የሚል ሰው ………ዕድሜውን ሙል እሺ ጌቶቼ፤ እሺ እመቤቶቼ ሲል የኖረ ሰው በድንገት ያንገሸግሸውና ዳግም ትእዛዝ አልቀበልም ብሎ እምቢ ይላል፡፡ እምቢ ሲልስ ምን ማለቱ ነው? የሚለውማ፤ ለምሳሌ ‹‹ይሄ ትእዛዝ በዛ፤ እስካሁን ድረስ እሺ ከእንግዲህ ግን አሻፈረኝ፤ መጠናችሁን አጣችሁ፤›› ወይም  ‹‹እሺ ለማለትና ለመቀበል በቃ ለማለትም ገደብ አለው:: እምቢተኛው የራሱን ድምጸ ውሳኔ ካገኘበት ጊዜ አንስቶ……. ከአሻፈረኝ ሌላ ቃል ባይወጣውም፤ መመኘትና መዳኘት ይጀምራል፡፡ እምቢተኛው የሚሰጠውን ትእዛዝ በመጋተር ሊቋቋመው ከሚችለው በላይ የሚጫንበትን ትእዛዝ ላለመቀበል ይወስናል፡፡›› የአፍሪካ ስፐሪንግ አፍሪካውያን ኢትዮጵያንም ጨምሮ፤ከተጫነባቸው የግፍ ጫና እንቅልፋቸው ነቅተው በብሩሁ ጸደይ  ተነቃቅተው ‹‹አሻፈረኝ! በቃ ማለት በቃ ነው!›› ማለት ሲችሉ ነው፡፡

በማርች 2012 ኢትዮጵያ ከዲክታተርሺፕ አገዛዝ ወደ ዴሞክራሲያዊ አስተዳደር ትሸጋገራለች ብዬ በድፍረት ተንብዬ ነበር፡፡. ከዚሁ ጋርም   የዲክተተርሺፕ ማብቃት፤ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲን መወለድ አያረጋግጥም ብዬም ነበር፡፡ከሚገረሰሰው የበሰበሰ ዲክታተርሺፕ ሊፈለፈል የሚችል የዴሞክራሲ ዕውነታ ሊኖር አይችልም፡፡ ዴሞክራሲን ለማምጣት በርካታ የሕብረት አድካሚ ስራዎች ያስፈልጉታል፡፡ኢትዮጵያን ከተጫነባት የፈላጭ ቆራጭ ዲክታተርሺፕ አገዛዝ ለማላቀቅና ከግፈኞችን በደል ከማይጠግቡ የዓመጻ ልጆች ለማላቀቅ ብዙ ጉልበትና አንድነት መስማማት ይጠይቃል፡፡ይህን ለማድረግ ደግሞ ዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ ተቋማት፤ተግባራዊነትን የሚያረጋግጥ የፖለቲካ ድርጅት፤የሲቪል ማሕበረሰብ ስርአት እና የብራሀን ፋና ወጊ የሆነ የነጻው ዴሞክራቲክ ፕሬስ ትንሳኤ የግድ አስፈላጊ ነው፡፡

በኤፕሪል 2012 ለጀግናዬና አልበገር ባዩ የፔን በነጻነት የመጻፍ ሽልማት አሸናፊ ለሆነው እስክንድር ነጋ አንድ ልዩ አክብሮት መግለጫ ጽፌ ነበር፡፡ እስክንድር ነጋ (ለኔ አይበገሬው እስክንድር ነጋ)ሽብርተኛ ተብሎ በኢትዮጵያ አለሁ በሚለው ገዢ መንግስት ለእስር ተዳርጓል፡፡ እስክንድር ግን የጀግኖች ጀግና ነው፡፡ የእስክንድር ለእስር መዳረግ በበርካታ ያገባናል በሚሉ ታዋቂ ጋዜጠኞች፤ በተመሳሳይ ስቃዩ በያሉበት የደረሰባቸው ኬነዝ ቤስት፤(የላይቤርያው ኢንድፔንዳንት ዴይሊ ጋዜጣ መስራች) ሊዲያ ካቾ፤ዝነኛው የሜክሲኮ ጋዜጠኛ፤ የኢራኩ እውቅ ተቃዋሚ፤አክባር ጋንጂ: ፋራጂ ሳርኮሂ፤በሕንዱ ታዋቂ አሩን ሹውሪ፤እና በበርካታ ሌሎች የእስሩ ተቃዋሚዎች ትኩረት ተሰጥቶታል፡፡ለኔ እስክንድር ልዩ ጀግናዬ ነው፤ ምክንያቱም፤ከሃሳብና ከእውነት ውጪ መሳርያ የሌለው ተሟጋች ነውና፡፡ ቅጥፈትን: በእውነት ስለት ብዕሩ ብቻ ሰየፈው:: ተስፋ መቁረጥን በተስፋ፤ፍርሃትን በድፍረት፤ ቁጣን በምክንያታዊነት፤ዕብሪትን በትህትና፤መሃይምነትን በዕውቀት፤አለመቻቻልን በትዕግስት፤ጥርጣሬን በዕምነት፤ ጭካኔን ደግሞ በርህራሄ እስክንድር ተዋጋው›፡፡ እስክንድር አልበገሬው!

በሜይ 2012  ላይ የጂ 8 የምግብ ዋስትና ስብሰባ በሚካሄድበት በዋሽንግቶን ዲ ሲ ወጣቱ ኢትዮጵያዊ ጋዜጠኛ አበበ ገላው ድምጹን ከፍ አድርጎ ነጻነት! እስክንድር ነጋ ይፈታ!  በማለት ድምጹን ከፍ አድርጎ ተናገረ!  ያለፈው መለስ ዜናዊ በዚያ በነበረበት ቦታ ላይ እንደተደገመባት ድመት አንገቱን ሰብሮ በዝምታ ወጣቱ ጋዜጠኛ፤ መለስ ዜናዊ ዲክታተር ነው ሲል ሰማው!  እስክንድር ነጋ ይፈታ! የፖለቲካ እስረኞች ይፈቱ! አንተ ዲክታተር ነህ መለስ! በማለት አበበ የተቃውሞ ጥሪውን አሰማ፡፡ አንተ በሰብአዊ ፍጡሮች ላይ ወንጀል ፈጽመሃል፤ ያለ ነጻነት ምግብ ዋጋ ቢስ ነው፤ የፖለቲካ እስረኞችን ልቀቅ! ነጻነት! ነጻነት! ነጻነት ያስፈልገናል! አለው፡፡ ለአሜሪካን ሕብረተሰብ የ‹‹ሄክለር ቬቶ›› በእጅጉ ክብር የሚያስገኝ መብት ነው፡፡ ሃሳቡ በጣም ቀላል ነው፡፡ምንግዜም መንግስታት ናቸው በሃሳባቸው የማይስማሙትንና ተቃዋሚዎቻቸውን ዝም ለማሰኘት ማፈኛ የሚያበጁ፡፡ ‹‹በሄክለር ቬቶ›› ደግሞ ግለሰቦች ጉልበተኛንና መንገስትን ዝም ጸጥ ማሰኘት ይችላሉ፡፡ ጠረጴዛው የግልብጥ ሆነ፡፡ መለስ ዜናዊ በአበበ ገላው ተለጉሞ ጸጥ እንዲል ተደረገ፡፡ አበበ ድሕረ  ገጽ መጠርያ ስሙ አዲስ ድምጽ ትርጉሙን በአግባቡ  አሳወቀበት ‹‹ድምጻቸው የታፈነባቸው ድምጽ››::

በጁን 2012 በሙስሊሙና በክርስቲያኑ የሃይሞነት መሪዎች ሊከፋፍሏቸው ባለሙት ላይ ባሳዩት ሕብረት ተገርሜ ነበር፡፡ በቶሮንቶ በስደት ላይ የሚገኙት፤ታዋቂው የሙስሊሙ እምነት ተከታዮች መሪ፤ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ትምህርት የሚሆን መልዕክት አስተላለፉ፡፡‹‹ እንደምታውቁት ኢትዮጵያ ብዙ እምነቶች የሚከበሩባት ሃገር ናት፡፡ኢትዮጵያ ፣ሙሊሙና የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ክርስቲያኖች በፍቅር ተከባብረው የኖሩባት ሃገር ለመሆኗ ታሪክ ይመሰክራል፡፡ አሁን እንኳነ 50ና 60 ዓመታት ጊዜ ውስጥ በኛው ዘመን፤አንዳችም ሁከትና አለመግባባት በመሃላቸው አይተን አናውቅም፡፡ ማንኛውንም ነገር የምናገኘው ሃገር ሲኖረን ነው፡፡ ሃይመኖት የግል ምርጫ ነው፡፡ ሃገር ደግሞ የጋራችን ነው:: ሃገር ከሌለ ሃይማኖትም አይኖርም፡፡……..እነሱ…ገዢዎቹ የገሃሪቱን መሬት ለውጭ ሰዎች ለባዕዳን እየሸጡት ነው፡፡ ተራፊውን ለም መሬትም ለራሳቸው ይዘውታል፡፡ ከሽያጩም የተገኘው ገንዘብ በሃገራችን አይቀመጥም፤ በግል ኪሳቸውና በሌላም ቦታ ባላቸው ኪሳቸው ነው፡፡ለመሆኑ አሁን የተረፈ ኢትዮጵያዊ ትውልድ አለ? በዩኒቬርሲቲ ለመማር የሚመዘገቡትም ቢሆኑ ሞራላቸው በተስፋ ማጣት ተዳክሟል፤በጫት ተለክፏል፤በሲጋራ ሱስ ተበክለዋል፤፡ ገዢው መንግስት ትውልዱን አጥፍተውታል፡፡

በጁላይ 2012 የፕሬዜዳንት ማንዴላን 94ኛ ዓመት የልደት በዓላቸውን በግሌ የአከባበር ስርአት አድርጌ ነበር፡፡ በጤንነትና በደስታ ረጂም ተጨማሪ ዓመታት እመኝላቸዋለሁ፡፡ ማዲባ ልክ እንደጋንዲ ለኔ ዋነኛ መኩሪያ የመንፈሴ አነሳሥ ናቸው፡፡ ማዲባና ጋንዲ ካለአንዳች ፍርሃት ዕውነትን ለባለስልጣናት ሲያውጁ ነበር፡፡ ለማዲባ፤ ጋንዲ፤ ማርቲን ሉተር ኪነግ: እውነተኛ የሰብአዊ መብት ተሟጋች፤ የፖለቲካ ፍላጎት ጨርሶ የሌለበት ነው:: የሰብአዊ መብት ፖለቲካ የሰብአዊ ክብር ነው እንጂ የፖለቲካ ዘይቤ፤የፖለቲካ መጎዳኘትም፤አለያም የፖለቲካ ስልጣን ፍቅር አይደለም፡፡ ቁርጠኛ የሆነ የሰብአዊ መብት ጠበቃ፤ለተሸለ ተስፋና ሕልም እውነታ የቆመ ነው፡፡እኔ ለብዙ ዓመታት በኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ጉዳይና በፈላጭ ቆራጭ ገዢዎች ላይ በርካታ መሟገቻ ጦማሮች አቅርቤያለሁ:: ይህ ጥረቴ ደግሞ አፋጣኝ ፖለቲካዊ ለውጥ ወይም አፋጣኝ መዋቅራዊ ለውጥ እንደሚያስገኙ እገምተለሁ፡፡ ይህንንም ለረጂም ጊዜ በማድረግ የቆየሁበት ሰበብ፤ስለሰብአዊ መብት መሟገት፤ መከራከር፤ ጥብቅና መቆም የገዢዎችን ድክመት ይፋ ማውጣት ልክ ስለሆነና ጥሩና የሞርል ጉዳይም ስለሆነ ነው፡፡

በኦገስት 2012 ይፋ ባልሆነና ባልታወቀ ሕመም በሞት ለተለየን መለስ ዜናዊ ስንብት አደረኩ፡፡ ስንብት ለመፃፍ በጣም አስቸጋሪ ነበር፡፡ ለሁለት መቶ ሰባ አምስት ሳምንታት፤አንድም ሳምንት ሳይታለፍ፤ለሁለት አሰርት ዓመታት ኢትዮጵያን ሲገዛ በነበረው ሰው ላይ ያደረሰውን በደልና የፈጸመውን ግፍ በተመለከተ በማጋለጥ በርካታ ጦማሮች አቅርቤያለሁ፡፡ በ2005 ያ ሁሉ የዜጎች ጭፍጨፋ ባይፈጸምና 200 ንጹሃን ዜጎች በጠራራ ጠሃይ በጎዳና ላይ ለሞት ባይዳረጉ፤ ከ800 በላይ ቁስለኛ ባይደረጉ፤መለስ ዜናዊንና እኔን የሚያገናኘን ጉዳይ አይኖረም ነበር::  ዕጣ ፈንታ መለስ በኢትዮጵያ ውስጥ ታሪካዊ ሚና እንዲጫወት መርጦት ነበር፡፡ ለ17 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ ዲክቴተር ሆኖ ሲገዛ የነበረ ውን ወታደራዊ ጁንታ አሸንፎ ከገቡት የቡድኑ መሪዎች አንዱ ነበር፡፡ በድል ወቅት መለስ ስለ ዴሞክራሲያዊ ተግባራዊነት ምሎ ተገዝቶ፤ ልማትን ለማፋጠንምና ሃገርን ለመገንባት ቃሉን ሰጥቶ ነበር፡፡ ግና ዓመታቱ እየጨመሩና እያለፉ ሲሄዱ ቁጥር መለስ ጨቋኝ እየሆነ፤ትዕግስቱ ቅጥ እያጣ፤ አምባገነናዊ ትምከተኛ እየሆነ፤ከተካው ገዢ የበለጠ ጨካኝና ጨቁአኝ እየሆነ መጣ፡፡ በመጨረሻዎቹ ዘመኑ ላይ ብዙ የደህንነት አባላት ካድሬዎች የሚታገዝ የፖለስ ስርአተ መንግስት ፈጠረ፡፡ ዜጎች እንዳይነቃነቁና በነጻ እንዳያስቡ ቁጥጥሩን አጠናከረ፡፡ የሲቪሉን ማህበረሰብ ተቋማትንና የነጻውን ፕሬስ አባላት መወንጀል ያዘ፡፡ በሃገሪቱ የሩቅ ገጠር ሳይቀር ዘልቀው በመግባት ሕዘቡ ላይ  የግፍ ጫናቸውን አራገፉበት፡፡ ከ21 ዓመታት በላይ መለስ ስልጣኑን የሙጢኝ ብሎ ከጫካው ይዞት የመጣውን የፍትሕን ሰይፍ በግሉና ለራሱ ብቻ ጨብጦ፤ለመበታተኛነት እያዋለው፤ ሃሳቡን የሚሞግቱትንና ተቃዋሚዎችን በማስፈራራትና በደጋፊዎቻቸው ላይ ውንጀላና መጉላላትን እያካሄደ ፍጹም አምባገነናዊ በመሆነ ኖረ፡፡ ስልጣንን ከምንም በላይ አድርጎ በማየት ዕድል ሰጥቶት የነበረውን ቀጠሮ ስቶ በኢትዮጵያ አቻ የሌለው መሪ ሊባል የሚችልበትን ቀጠሮ አፋለሰ፡፡

በሴፕቴምበር 2012 የፕሬዜዳንት ኦባማን ዳግም ምርጫ ለምን እንደደገፍኩት አስረዳሁ፡፡ በመጀመርያ የምርጫ ዐመታቸው በአፍሪክ ውስጥ ስለነበራቸው አመለካከትና እንቅስቃሴ የሰብአዊ መብት መደፈር ቅሬታ ቢኖረኝም፤የፕሬዜዳንቱን ድጋሚ ምርጫ የመደገፌን መነሾ በሚገባ ገልጫለሁ፡፡ ፕሬዜዳንት ኦባማ በገቡት ቃል መሰረት ለአፍሪካ መልካም አስተዳደር የሰብአዊ መብት መከበርን፤ ዴሞክራሲያዊ ሁኔታን አስገኝተዋል? በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት መከበርን አረጋግጠዋል? በጭራሽ! ፕሬዜዳንት ኦባማ በአክራ ጋና በገቡት ቃል መሰረት ምንም ባለማድረጋቸውና ቃላቸውን ባለመጠበቃቸው ኢትዮጵያዊያን አሜርካዊያን ቅር ተሰኝተዋል:: አስተዳደራቸውስ በኢትዮጵያ ላለው ዲክታተራዊ ገዢዎች ስለሚያደርገው ድጋፍስ፤ አዎን እናስታውሳለን ፕሬዜዳንት ኦባማ ያን የመሰለ ንግግር በማድረግ በአፍሪካ ውስጥ ጠንካራና ጤናማ አስተዳደር እንደሚያስፈልግ አድርገው እንደነበር፡፡ ሁላችንም ይህን አስመልክተው ምን እንዳሉ የምናስታውሰው ነው፡፡ ‹‹አፍሪካ ጡንቻማ መሪዎች አይደሉም የሚያስፈልጓት፤ የፈረጠመና መልካም አስተዳደራዊ ተቋም እንጂ›› ‹‹ልማት መሰረቱ መልካም አስተዳደር ነው›› ገዢዎች ኤኮኖሚውን የሚበዘብዙት ሃገር ጨርሶ ሊለማ አይችልም›› እነዚህን ቃላቶች ለይስሙላ ያሉዋቸው ናቸው ወይስ ከምር አምነውባቸው? ዕውነቱ መውጣት አለበት፤ ፕሬዜዳንቱ ያደረጉት አለያም ያላደረጉት መልካም አስተዳደርን፤ዴሞክራሲያዊ ስርአትን፤የሰብአዊ መብት መከበርን በኢትዮጵያ አለማስገኘቱ፤ እኛ እራሳችን ባለጉዳዮቹ በርካታ ቁጥር ያለን ኢትዮጵያዊያን አሜሪካውያን ያደረግነው አለያም ያላደረግነው ጋር የተለያየ አይደለም፡፡ ይሄ ነው የሚጎመዝዘው እውነትና መቀበልና ማመን ያለብን፡፡

በኦክቶበር 2012 ስለሴቶችና ጡት ካንሰር ጥንቃቄ በኢትዮጵያ አንድ ጦማር አቅርቤ ነበር፡፡ በሃገር ውስጥም ሆነ በዲያስፖራው ኢትዮጵያዊያን መሃል ስለ አንዳንድ በሽታዎች ሚስጥራዊነት ጎጂ ባሕል አለን፡፡ ሁለቱ በድብቅ የተከተቱ በሽታዎች ካንሰርና ኤች አይ ቪ ኤይድስ ናቸው፡፡ባህሉም በሽታዎቹን እስከመጨረሻው ድረስ: ከሞትም በኋላ ደመደብቅ ነው፡፡ ይህን አስከፊና አሳዛኝ ባህል በቅርቡ በመለስ ዜናዊ ሞት መስክረነዋል፡፡ የመለስ በሽታና የሞቱ መንስኤ ሚስጥራዊነቱ በጥብቅ የሚጠበቅ የሃገር ሚስጢር ሆኗል፡፡ በስፋት እንደሚታመነው የሞተው በአእምሮ ካንሰር ነው ይባላል፡፡ ይህ በሚስጢር የመያዝ ባህላችን በርካታ ኢትዮጵያዊያኖችን ለሕልፈተ ሞት ዳርጓል፡፡ ለምሳሌ በአሜሪካን ሃገር በጉልህ የሚታወቅና የታይ የሕመም መደበቅ ባህላችን በርካታ ወገኖቻችንን ለሞት ዳርጓል፤ በዚህም ሳቢያ ብዙዎች ቅድመ ምርመራ በማድረግ በጊዜው ሊደርሱበት የሚችሉትን በሽታቸውን በሚስጢር በመያዝና ቅድመ ምርመራውም የሚያስከትለውን ውጤት ለማወቅ ካለመፈለግና በመፈራት በርካቶች ለሞት ተዳርገዋል፡፡ ካንሰርን በተመለከተ ሚስጥር ማድረግን ቅድመ ምርመራን አለማድረግ በራስ ላይ የሞት ደረሰኝ እንደመቁረጥ ያለ ነው፡፡

በኖቬምበር 2012 ማስታወሻዬ፡፡ በጁን 6-8 እና በኖቬምበር 1-4 በመለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትእዛዝና ቁጥጥር በዚያው ዓመት በሜይ የተካሄደውን ፓርላማዊ ምርጫ አስመልክቶ መብትና ሕገመንግስት ይከበርልን በማለት ባዶ እጃቸውን አደባባይ የወጡትን ንጹሃን ዜጎች ጭፍጨፋና ግፋዊ ግድያ አስታወስኩ፡፡ ሕጋዊ ሆኖ የተመረጠው አጣሪ ኮሚሽን ይፋ ባደረገው ዘገባ ባቀረበው መሰረት ከሰላማዊ ሰልፈኞቹ መሃል የመንግስት ሚዲያ እንዳለው አንድም ሰው ጠመንጃም/ሽጉጥ አለያም የእጅ ቦንብ የያዘ አልነበረም፡፡ በመንግስት ወታደሮችና የደህንነት ሰዎች የተተኮሱት ጥይቶች ሰልፈኛውን ለመበተን ተብለው የታለሙ ሳይሆኑ ደረትና ጭንቅላት ላይ ለመግደል ተብለው የተተኮሱ ነበሩ፡፡ ‹‹በወቅቱ የ29 ዓመቱን ኢትዮጵያዊ መምህርና የሰብአዊ መብት ተሟጋችና በደቡብ ኢትዮጵያ በ11/11/11 እራሱን በእሳት አቃጥሎ የተሰዋውን የዳውሮ ዞን ነዋሪውን የኔሰው ገብሬንም አስታውሻለሁ፡፡ የኔ ሰው በደረሰበት ቃጠሎ ከሶስት ቀናት በኋላ በሆስፒታል ሕይወቱ አልፏል፡፡ በስብሰባው አዳራሽ በራፍ ላይ ለነበሩትም ያስተላለፈው መልዕክት ‹‹መልካም አስተዳደርና ፍትሕ በሌለበት ሃገር፤ ሰብአዊ መብት በማይከበርበት ሃገር፤ እነዚህ ወጣቶች ነጻ እንዲሆኑ እኔ እራሴን አቃጥላለሁ›› ነበር፡፡

በዲሴምበር 2012 የሱዛን ራይስን የአሜሪካ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሹመትን በጥብቅ ተቃዉሜ ነበር፡፡ የወቅቱ የአሜሪካ የተባበሩት መንግስታት አምባሳደር፤ ከዘመነኞቹ የአፍሪካ ፈላጭ ቆራጭ ገዢዎች ጋር በሚፈጥሙት ግፍና በደል ሙዚቃ አብራቸው እስክስታዋን ሱዛን ራይስ ታቀልጠው ነበር፡፡ በኤፕሪል 6 በሩዋንዳ ተቀስቅሶ ያለውንና በሚሊሺያዎች የተነሳሳውን ኢንተርሃምዌ: ራይስና ሌሎችም የአሜሪካን ባለስልጣናት አስቀድመው አውቀውት ነበር፡፡ በሩዋንዳ ከሚገኘው የተባበሩት መንግስታት ቢሮ ስለ ጉዳዩ የእለት ተእለት መግለጫ ይደርሳቸው ነበር፡፡ በዚህም ባለስልጣኖቹ የዘር ማጥፋት ሂደት መጸነሱን አውቀውታል፡፡ በአዲስ አበባ በሴፕቴምበር 2 እና በኒውዮርክ በተካሄደው የመለስ ዜናዊ ሞት መታሰቢያ ስንብት ያቀረበችው  ከንቱ ውደሴ በእጅጉ አሳፋሪና ከአንድ የመንግስት ተወካይ ከፍተኛ ባለስልጣን የማይጠበቅ ነበር፡፡ ራይስ በመለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትእዛዝ ለሞት የተዳረጉትን ንጹሃን ዜጎች ከምንም አልቆጠረቻቸውም፡፡ በመለስ ትእዛዝ በወህኒ ሃሳባቸውን ስለገለጹና ሕዝብ ማወቅ ያለበትን ስላሳወቁ፤ የመንግስትን ሕጸጽ ይፋ ስላወጡ ብቻ ሕገመንግስታዊና ሰብአዊ መብታቸው ተገፎ ለወህኒ የተዳረጉትን ሁሉ ችላ ከማለት ባለፈ ትታቸዋለች፡፡ራይስ በሩዋንዳ የተፈጸመውን ግድያና ጭፍጨፋ ሆን ብላ ላለማየት አሁንም ካለፈ በኋላ ላለማስታወስ አይኗን ጨፍናለች፡፡ በኢትዮጵያም የተካሄደውንና እሁንም በመካሄድ ላይ ያለውን ጭፍጨፋ ግፍና በደል ግድያ እስራት እያወቀችና እየተረዳች አይኔን ግንባር ያድርገው ብላ ክዳለች፡፡ አሜሪካ ‹‹እያየሁ አላየሁም;; ‹‹እየሰማሁ አልሰማሁም›› ‹‹ብናገርም አልተነፈስኩም›› የሚል የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አያስፈልጋትም፡፡ አሜሪካ የሚያስፈልጋት የሃገር እስተዳዳር፤ በሰብአዊ መብትና በመንግስት ሕገወጥነት መሃል ያለውን ልዩነት የሚመለከትና የሚያውቅ የዉጭ ጉዳይ አስተዳዳሪ ነው የሚያስፈልጋት፡፡

እንጠራራ! ለሁሉም ሰብአዊ ፍጡራን ሰላምና ደህንነት በ2013፡፡ ሁላችንም ስለሰብአዊ መብት መከበርና የመንግስታትን እኩይ ተግባር በማጋለጥ ረገድ አብረን እንንቀሳቀስ!

ፕሮፌስር ዓለማየሁ ገብረማርያም በካሊፎርኒያ ስቴት ዩኒቨርሲቲ ሳን በርናርዲኆ የፖሊቲካ ሳይንስ መምሀርና የህግ ጠበቃ ናችው።

*የተቶረገመው ጽሁፍ (translated from):  http://open.salon.com/blog/almariam/2012/12/29/ring_in_redress_to_all_humankind

(ይህን ጦማር ለሌሎችም ያካፍሉ::) ካሁን በፊት የቀረቡ የጸሃፊው ጦማሮችን  ለማግኘት እዚህ ይጫኑ::

http://www.ecadforum.com/Amharic/archives/category/al-mariam-amharic 

http://ethioforum.org/?cat=24