የእነ አቶ አባይነህ ጉባኤ በአሉባልታ ተጠናቀቀ

በቀድሞው የመኢአድ ቢሮ የሚገኙትና ከቅንጅት ህገ ደንብ ውጭ የአቶ ሀይሉ ሻውል ወኪል ሆነው በተሾሙት በአቶ አባይነህ ብርሃኑ የሚመሩት አባላት ደጋፊዎቻቸውን ለማነጋገር በተዘዋወሩባቸው ክልሎች ያጋጠሟቸውን ጉዳዮች አስመልክቶ በዛሬው እለት በጽ/ቤቱ የቃል ሪፖርት ማቅረባቸውን የውስጥ ምንጮች ለዜና አገልግሎቱ ገለጹ፡፡

ደጋፊዎቻቸውን የማነጋገር ተልእኮ ተሰጥቷቸው በተለያዩ ክልሎች የተጓዙት እነዚህ አባላት ያጋጠሟቸውን ችግሮች ሲገልጹ በዋንኛነት ያነሱት በፕሬዝዳንቱ ታግደዋል የተባሉት የአመራር አባላት ጉዳይ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ከወቅቱ አስቸጋሪነት የተነሳ ደጋፊዎችን ማነጋገር ብቻውን እንኳ ፈታኝ የነበረ ቢሆንም በአንድነት ትግሉን የሚመሩ አባላትን አግጃለሁ ማለቱ አብዛኛውን ደጋፊ ያስቆጣና ለገዢው ፓርቲ ያልታሰበ (አንድ የደሴ ነዋሪ አባባል) ሀይሉ ሻውል ለወያኔ ያቀረቡት የሚሌኒየም ስጦታ ነው በማለት ተችተውት እንደነበር አንድ ልኡክ በቅሬታ አንስተዋል:: ይህም ዋንኛው ልኡካኑን በየደረሱበት በተጠየቅ የሞገተ ጉዳይ እንደነበር የቃል ሪፖርቱን ያቀረቡት አባላት ሳይሸሽጉ ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ህዝብ እስካሁን ሊገታ ባልቻለ ወከባና እንግልት ውስጥ የገባበትን ትግል በቀድሞው የመኢአድ ቢሮ በመመሸግና ሊቀ መንበራቸውን ስጋት ውስጥ የሚከቱ የተሳሳቱ መረጃዎች በማቅረብ ስሜታዊውንና እንዴት የቅንጅት መሪ ሆነው ተመረጡ የሚል ጥያቄ በህዝቡ አእምሮ የፈጠሩትን ሀይሉ ሻውልን የሚጠቀሙባቸው የአቶ አባይነህ ቡድኖች ሪፖርቱ እንዲሰማ ያደረጉበት ዋንኛ ምክንያት በሩቅ ርቀት በመሾምና በመሻር ላይ ያሉትን ፕሬዝዳንት አስፈቅደው ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ ለማድረግ መሆኑን ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡

ጉባኤው ሲጀመር ስርአት ያለው ስብሰባ የመሰለ ቢሆንም በወ/ት ብርቱካን የሚመራው የስራ አስፈጻሚ ቡድን ሲነሳ ግን በጣም አስገራሚ ወደሚባል አሉባልታና ምክንያታዊ ወዳልሆኑ ዘለፋዎች በመግባት ረዥም ሰአታትን አሳልፈዋል፡፡