ለቅንጅት እንዳይቀሰቅሱ የተሰጉ አንድ ተመራጭ በተለያዩ ክሶች እየተንገላቱ ነው

በ3ኛው አገር አቀፍ ምርጫ ቅንጅትን በመወከል ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ያለፉትና በተመረጡበት ጎጃም ውስጥ ህዝቡን በማስተባበር ታዋቂ የሆኑት አቶ ይታየው ጥሩነህ ከእስር ለተፈቱት የቅንጅት አመራሮች በመወገን ሊቀሰቅሱ ይችላሉ በሚል የፈጠራ ክሶች እየቀረቡባቸው መሆኑን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ለዜና አገልግሎቱ ገለጹ፡፡

አመራሩ ከእስር ከመውጣቱ በፊት የገዢው ፓርቲ ካድሬዎች ቅንጅትን በመወከል ፓርላማ የገቡ ግለሰቦችን በማስፈራርያና በመደለያ ወደተለያዩ ቡድኖች እንዲቀላቀሉ ሲያደርጉ የቆዩ ሲሆን ተወካዩ የቀረቡላቸው የተለያዩ አንጃዎች የቅንጅቱን ተልእኮ ያነገቡ አይደሉም በሚል በገለልተኝነት የቆዩና አቋማቸውን በማሳወቅ በፓርላማው ውስጥ በድምጸ ተአቅቦ የተቀመጡ ሲሆን ከአመራሩ መፈታት በኋላ ለቅንጅቱ ይቀሰቅሳሉ በሚል የ16 አመት ታዳጊ ደፍረዋል የሚል የፈጠራ ክስ ተመስርቶባቸው ቆይተዋል፡፡ ይሁንና ተደፍራለች የተባለችው ወጣት ከዚህ ቀደም አግብታ የነበረች መሆኗን፤ በግለሰቡ ያለመደፈሯንና ጉዳዩ ፖለቲካዊ ጫወታ መሆኑን በመግለጽ ለተወካዮች ም/ቤት አፈ ጉባኤ ጽ/ቤት፤/ ወ/ሮ ነጻነት አስፋውን በግል በማነጋገር ጭምር ምርመራውን ለያዘው የቦሌ ክ/ከተማ ፖሊስ፤ ለሴቶች ጉዳይ ጽ/ቤትና ለመሳሰሉት ብታቀርብም ፖለቲካዊ ብትሩ ግን በግለሰቡ ላይ እስካሁን መቀጠሉን ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡

ተመራጩ በዛሬው እለት በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 7ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡ ቢሆንም በሁኔታው ግራ የተጋቡት ዳኛና አቃቤ ህግ በወ/መ/ቁ 97439 ቁጥር 988/06/99 የተያዘውን የክስ መዝገብ ለሁለተኛ ግዜ ተጠቂ እስክትቀርብ በሚል ዘግተዋል፡፡

ሁኔታውን በጥልቀት የሚያውቁ የቅንጅቱ ቤተሰቦች በዛሬው እለት የታየውን ችሎት ለመታደም በልደታ ፍርድ ቤት መሰብሰብ የጀመሩት ከጠዋቱ 2፡00 ሰአት ጀምሮ ሲሆን አዳራሹ ስላልበቃ ውጤቱን ውጭ በመሆን ሲጠባበቁ ታይተዋል፡፡