የምርጫ ካርድ አንወስድም ያሉ የአንድ ቤተሰብ አባላት ታሰሩ

በምስራቅ ሸዋ ዞን ዝዋይ ከተማ ቀበሌ 02 የሚኖሩና በንግድ ስራ የሚተዳደሩ አራት የቤተሰብ አባላት በሚያዝያ ለሚካሄደው ምርጫ ካርድ አንወስድም በማለታቸው በታጣቂዎች ተወስደው መታሰራቸውን ሪፖርተራችን ከስፍራው ዘገበ፡፡

ወራት የቀሩትና ተመዝጋቢ በማጣት እስከቀጣዩ ወር መጀመርያ የተራዘመውን የመራጮች ምዝገባ ለመቀስቀስ በየቤቱ መዞር የጀመሩት የዝዋይ ከተማ የምርጫ አስተባባሪዎች በየቤቱ በመዞር ነዋሪዎቹ የመምረጫ ካርድ መውሰዳቸውን መጠየቅ የጀመሩት ባለፈው ሳምንት መጀመርያ ላይ መሆኑን ዘገባው ያመለከተ ሲሆን ትናንት ማምሻው ላይ በተለመደው ተግባር ላይ ተሰማርተው ማስፈራርያ የተሞላባቸው መጠይቆችን ሲያደርጉ በ02 ቀበሌ ጅንአድ ጀርባ የሚኖሩትና በንግድ ስራ ላይ የተሰማሩት አቶ ግዛው አበጋዝ የምርጫ ካርድ ያለመውሰድ መብት አለኝ በማለት ባነሱት የመብት ጥያቄ በተፈጠረ ውዝግብ ከሁለት ልጆቻቸውና በግሮሰሪያቸው ውስጥ ከሚረዳቸው ዘመዳቸው ጋር ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወስደው እስከዛሬ ከሰአት በኋላ ከቆዩ በኋላ በዋስ ተለቀዋል፡፡

የቅንጅት ተወዳዳሪዎች በምርጫ 97 ወቅት ባሳዩት ከፍተኛ ተሳትፎ ለምርጫው ልዩ ተነሳሽነት አሳይቶ የነበረው መራጭ ህዝብ ሂደቱ ባልታሰበ መንገድ ተደነቃቅፎ ከቀረ በኋላና በተለይም የዝዋይ ህዝብ በመረጣቸው የቅንጅቱ ተወካይ ፋንታ ኦህዴድን ወክለው የተወዳደሩት ግለሰብ በማጭበርበር ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ካለፉ በኋላ ቀጣዩ የማሟያ ምርጫ ትኩረት መሳብ እንዳልቻለ የከተማዋን ነዋሪዎች አስተያየት ዋቢ ያደረገው ዘገባ ያመለክታል፡፡

በከተማዋ ኦህዴድን በመወከል የተወዳደሩትና በከፍተኛ የድምጽ ልዩነት የተሸነፉት የዝዋይ ከፍተኛ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ም/ር/መምህር የሆኑት አቶ ሚሊዮን ጋረደው ብሩ የሚባሉ ግለሰብ እንደሆኑ ከትናንቱ አሳፋሪ ክስተት በኋላ ዘጋቢያችን ያነጋገራቸው ነዋሪዎች የጠቆሙ ሲሆኑ ቅንጅቱን በመወከል ያሸነፉት ተወዳዳሪ እንዲሸማቀቁ የሚያደርጉ ጫናዎች ሲደረጉባቸው እንደከረሙ ተገልጧል፡፡